፮ - “ወደ ፈተናም አታግባን"
- Category: በሰማያት የምትኖር አባታችን ሆይ ጸሎት ሰባት ልመናዎች
- Published: Thursday, 13 October 2011 19:16
- Written by Super User
- Hits: 5266
- 13 Oct
፮ - “ወደ ፈተናም አታግባን"
ኃጢአቶቻችን በፈተና ከመውደቃችን የሚመነጩ ስለሆኑ ይህ ልመና ከቀደመው መንስኤ ጋር ተያያዥነት አለው፡፡ ስለዚህም አባታችንን ወደ ፈተና “እንዳያስገባን” እንለምነዋለን፡፡ የግሪኩን ግሥ በነጠላ /በአንድ የእግሊዝኛ ቃር መተርጐም ያስቸግራል፤ የግሪኩ ቃል “ወደ ፈተና እንገባ ዘንድ አትፍቀድ” እና “በፈተና እንድንወድቅ አታድርግ” የሚል ሁለት ትርጉም አለው፡፡ “እግዚአብሔር በክፉ አይፈትንም፤ አርሱ ራሱ ማንንም አይፈትንም፡፡” ይልቁንም በተፃራሪው ከክፉ ነገር ነጻ ሊያወጣን ይፈልጋል፡፡ ወደ ኃጢአት የሚመራንን መንገድ እንከተል ዘንድ እንዳይፈቅድ እንለምነዋለን፡፡ “በሥጋና በመንፈስ” መካከል በሚካሄድ ጦርነት ውስጥ እንገኛለን፤ ይህ ልመና የማወቅንና የብርታትን መንፈስ ይማጸናል፡፡
መንፈስ ቅዱስ ለውስጣዊው ሰው ዕደገት በሚያስፈልጉት መከራዎች እንዲሁም ወደ ኃጢአትና ሞት በሚመራው ፈተና መካከል እንድንለይ ያደርገናል፡፡ በመፈተንና በፈተና በውደቅ መካከል ያለውን ሁኔታ ለይተን ማወቅ አለብን፡፡ በመጨረሻም ውጤቱ ሞት ሆኖ ሳለ ዓላማው “ዓይንን የሚያስደስት” መልካምና ተፈላጊ መስሎ የሚታየውን የፈተናን ሐሰተኝነት ማስተዋል እርቃኑን ያስቀረዋል፡፡
እግዚአብሔር ነጻ ፍጡራንን ይሻል እንጂ መልካሙን እንድንቀበል አያስገድደንም፡፡ ፈተና የሚሰጠን አንዳንድ ጥቅም አለው፡፡ ነፍሳችን ከእግዚአብሔር የተቀበለችውን ነገር ከአምላክ በስተቀር እኛም ራሳችን ብንሆን እንኳ አናውቀውም፡፡ ነገር ግን ፈተና እኛ ራሳችንን ማወቅ እንችል ዘንድ ይህንኑ ይገልጽልናል፤ በዚህም መሠረት እኛ ክፉ ዝንባሌያችንን እናውቃለን፤ ስለሆነም ፈተና ስለገለጸልን በጐነት ሁሉ ምሥጋና ልናቀርብ ይገባናል፡፡
“ወደ ፈተና አታግባን” የሚለው ሐረግ የልብን ውሳኔ ያመለክታል፡፡ “መዝገብን ባለበት ልብህም በዚያ ይሆናል… ለሁለት ጌቶች መገዛት የሚቻለው ማንም የለም፡፡” ማቴ 6፡21-24 “በመንፈስ ብንኖር በመንፈስ እንመላለስ፡፡” ገላ 5፡25 ከመንፈስ ቅዱስ ጋር በሚሆን በዚህ ስምምነት አብ ጥንካሬን ይሰጠናል፡፡ “ለሰው ሁሉ ከሚሆነው በቀር ምንም ፈተና አልደረሰባችሁም፤ ነገር ግን ከሚቻላችሁ መጠን ይልቅ ትፈተኑ ዘንድ የማይፈቅዱ እግዚአብሔር የታመነ ነው፤ ትታገሱም ዘንድ እንድትችሉ ከፈተናው ጋር መውጫውን ደግሞ ያደርግላችኋል፡፡” 1ቆሮ 1ዐ፡13
እንዲህ ዓይነት ተጋድሎ እንዲህ ዓይነት ድል ሊገኝ የሚችለው በጸሎት ብቻ ነው፡፡ ኢየሱስ ተልአኮውን በይፋ ሲጀምርና በመጨረሻ ስቃዩ ባደረገው ትግል ፈታኙን ድል የነሣው በጸሎት ነው፡፡ ለሰማያዊው አባታችን በምናቀርበው በዚህ ልመና ክርስቶስ ከተጋድሎውና ከስቃዩ ጋር አንድ ያደርገናል፡፡ እርሱ ከእርሱ ልብ ጋር ንቃት አንዲኖረን ይጠራናል፡፡ ንቃት “የልብ ጠባቂ” ነው፤ ኢየሱስም አብን ስለ እኛ ሲለምን “በስምህ ጠብቃቸው” ዮሐ 17፡11 ይላል፡፡ መንፈስ ቅዱስ ዘወትር ነቅተን እንድንጠባበቅ ይሻል፡፡ በመጨረሻም ይህ ልመና በምድራዊ ተጋድሏችን ከሚሆነው ከመጨረሻው ፈተናችን ጋር በተዛመደ መልኩ ልዩ ትርጉሙን ያገኛል፡፡ የመጨረሻውን ጽናት ይጠይቃል፡፡ “እነሆ እንደ ሌባ ሆኜ እመጣለሁ፤ ነቅቶ የሚጠባበቅ ሰው ምስጉን ነው፡፡” ራዕ 16፡15
/የካቶሊክ ቤተክርስቲያን ትምህርተ ክርስቶስ ከቁጥር 2846-2849/