እኛ ማነን

በኢትዮጵያ ካቶሊካዊት ቤተክርስቲያን ሥር የምንገኝ ሲታውያን መነኮሳን በአገራችን በአዲስ አበባ፣ በመንዲዳ፣ በሆሣዕናና በጎንደር ገዳማት ሲኖሩን፤ ዓላማችንም በወንጌል ላይ የተመሠረተውን የቅዱስ አቡነ ቡሩክ ደንብን (The Rule of St. Benedict) በመከተል ክርሰቲያናዊ የጥምቀት ጸጋችንን በምልአት በሲታዊ ትውፊት መኖር ነው።.....

ይህም በምንኩስና ሕይወታችን፤ በግላዊም ሆነ ማኅበራዊ ጸሎትና ሥራ በቀጣይነት እግዚአብሔርን የመፈለግና የማመስገን ሕይወት ነው። በአጭር ቃላት ሕይወታችን “ጸሎትና ሥራ” (Ora et Labora) በሚለው ዘመን ጠገብ ትውፊታችን ይገለጻል።

ለዚህም ግብ መሳካት “ከክርስቶስ ፍቅር ምንም ነገር ያለማስበለጥ” የሚለውን ደንባችንን በማሰላሰል ለእግዚአብሔር መንግሥት መስፋትና ምስክርነት በጸጋው ተማምነን ለመኖር የወሰንን ነን።

በካቶሊክ ቤተ ክርስቲያን እምነት መንፈሳዊ ትምህርቶች፣ የመጽሐፍ ቅዱስ ጥናት፣ ታሪክ፣ ሥርዓተ አምልኮ፣ ጸሎቶችና መንፈሳዊነትን ወደ ምንካፈልበት፤ የቤተ ክርስቲያናችን ዜና ወደ ሚነገርበት፣ እንዲሁም በተቀደሰ ጋብቻም ሆነ በምንኩስና ሕይወት ወደ ቅድስና ጥሪ ለመጓዝ የሚያግዙ እውነታዎች ወደሚጋሩበት፣ የቅዱሳን ሕይወት፣ ሀብትና ትሩፋት ወደ ሚነገርበት፣ ባጠቃላይ የአምላካችን መልካም ዜና ወደሚታወጅበት ይህ ድረ ገጽ እንኳን በደህና መጡ!!

ከመ በኲሉ ይሴባሕ እግዚአብሔር!- እግዚአብሔር በነገር ሁሉ ይከብር ዘንድ፤ አሜን።1ጴጥ.4:11

Map St Joseph Cistercians

Top Panel

መደምደምያ

መደምደምያ

በጥናታችን ፡ መነሻ ፡ ላይ ፡ አምስት ፡ እንጀራ ፡ እና ፡ ሁለት ፡ ዓሣ ፡ አባዝቶ ፡ ቁጥራቸው ፡ ከአምስት ፡ ሺህ ፡ በላይ ፡ ለሆኑ ፡ ሰዎች ፡ መግቦ ፡ አሥራ ፡ ሁለት ፡ መሶብ ፡ ያህል ፡ ቁርስራሽ ፡ መሰብሰብ ፡ እንደ ፡ ታምራት ፡ ወይስ ፡ አንደ ፡ አስማት ፡ ይቆጠራል ፡ የሚለውን ፡ ሀሳብ ፡ አንስተን ፡ ነበር ፡፡ በጥናታችንም ፡ ሂደት ፡ ላይ ፡ ታሪኩን ፡ በተለያየ ፡ መልኩ ፡ ለማብራራትና ፡ ለመረዳትም ፡ ሞክረናል ፡፡ አብዛኞቻችን ፡ በጥናቱ ፡ ውስጥ ፡ ለጥያቄው ፡ መልስ ፡ የሚሆነን ፡ ማብራሪያ ፡ አግኝተን ፡ ይሆናል ፡፡ በተለይም ፡ ከምሥጢረ ፡ ቅ.ቁርባን ፡ ጋር ፡ በተያያዘ ፡ መልኩ ፡ በተደረገው ፡ ገለጻ ፡ ታሪኩን ፡ የበለጠ ፡ ለመረዳት ፡ ይጠቅማል ፡ ብለን ፡ እናምናለን ፡፡

አሁንም ፡ አስቲ ፡ ጌ.ኢ.ክ ፡ ይህንን ፡ ታምራት ፡ አላከናወነም ፤ ይህ ፡ ታሪክ ፡ ሌላ ፡ ተጨማሪ ፡ የሆነ ፡ የተሸሸገ ፡ መልእክት ፡ አለው ፡ እንጂ ፡ እንዲያው ፡ እንጀራና ፡ ዳቦ ፡ አባዝቶ ፡ አብልቶና ፡ አጥግቦ ፡ አሥራ ፡ ሁለት ፡ መሶብ ፡ ቁርስራሽ ፡ ሰበሰበ ፡ ብንል ፡ አስማተኝነትን ፡ ያሳያል ፡ እንጂ ፡ ታምራትን ፡ አያሳይም ፡ የሚሉትን ፡ የመጽሐፍ ፡ ቅዱስ ፡ ሊቃውንቶች ፡ ሀሳብ ፡ እናክልበት ፡፡ እንደነዚህ ፡ ሊቃውንቶች ፡ አገላለጽ ፡ በወቅቱ ፡ ኢየሱስ ፡ ያስተምረው ፡ የነበረው ፡ ሕዝብ ፡ በጣም ፡ ራስ ፡ ወዳድ ፡ የሆነ ፣ ለራሱ ፡ ብቻ ፡ የሚኖር ፣ ተከፋፍሎ ፡ መብላትን ፡ የማያውቅና ፡ የወንድማማችነትን ፡ ፍቅር ፡ የራቀው ፡ ሀይለኛ ፡ የሆነ ፡ ማህበረሰብ ፡ እንደነበር ፡ ይገልጻሉ ፡፡ ይህ ፡ ሕዝብ ፡ ታድያ ፡ ወደ ፡ አንድ ፡ የስብሰባ ፡ ቦታ ፡ ወይም ፡ ከአካባቢው ፡ ራቅ ፡ ብሎ ፡ ሲሄድ ፡ የየራሱ ፡ የሆነ ፡ የሚበላ ፡ ነገር ፡ ይዞ ፡ ይንቀሳቀስ ፡ ነበር ፡፡ የያዘውንም ፡ ምግብ ፡ ይሞታታል ፡ እንጂ ፡ በምንም ፡ ይሁን ፡ በምንም ፡ ጉዳይ ፡ ከሌላው ፡ ጋር ፡ ተከፋፍሎ ፡ አይበላውም ፡ ነበር ፡፡ የኢየሱስንም ፡ ትምህርት ፡ ለመከታተል ፡ ቀዬአቸውን ፡ ጥለው ፡ ራቅ  ወዳለው ፡ ተራራ ፡ ለረጅም ፡ ሰዓት ፡ ከሱ ፡ ጋር ፡ ወይም ፡ እሱን ፡ እያደመጡት ፡ ለመቆየት ፡ ሲሄዱም ፡ እያንዳንዱ ፡ የራሱ ፡ የሆነ ፡ ምግብ ፡ ይዞ ፡ ነበር ፡ የሚሄደው ፡፡ እነዚህ ፡ ሕዝቦች ፡ ታድያ ፡ ለረዥም ፡ ሰዓታት ፡ ኢየሱስን ፡ ሲያደምጡ ፡ ቆይተዋል ፤ ስለምን ፡ ግን ፡ እንዳስተማራቸው ፡ በወንጌሉ ፡ አልተገለጸም ፡፡ በእርግጥ ፡ በአዲስ ፡ ኪዳን ፡ ውስጥ ፡ ያለው ፡ ጌ.ኢ.ክ. ያስተማረው ፡ ትምህርት ፡ በሙሉ ፡ ባጭሩ ፡ ቢገለጽ ፡ ሁለት ፡ ነገሮች ፡ ብቻ ፡ ናቸው ፡፡ እነዚህም ፡ የእግዚአብሔር ፡ ፍቅርና ፡ የባልንጀራ ፡ ፍቅር ፡ ናቸው ፡፡ እነዚህ ፡ በምንም ፡ መልኩ ፡ የማይለያዩ ፡ የ.ጌ.ኢ.ክ ፡ ትምህርቶች ፡ ፍቅር ፡ ወደ ፡ ላይ ፡ እና ፡ ፍቅር ፡ ወደ ፡ ጎን ፡ በመባልም ፡ በጌ.ኢ.ክ ፡ መስቀልም ፡ ይመሰላሉ ፡፡ ይህም ፡ ጌ.ኢ.ክ. እጆቹን ፡ ወደ ፡ ጎን ፡ ተደርጎ ፡ መስቀል ፡ ላይ ፡ መቸንከሩን ፡ በባልንጀራ ፡ ፈቅር ፡ ሲገለጽ ፡ እራሱንና ፡ እገሮቹን ፡ ወደ ፡ ላይና ፡ ወደ ፡ ታች ፡ መሆናቸው ፡ ደግሞ ፡ የእግዚአበሔር ፡ ፍቅር ፡ መግለጹን ፡ ነው ፡፡ ከዚህም ፡ በተጨማሪ ፡ አንድምታ ፡ ዮሐ 14 ፡ 21 ፡ አምስቱ ፡ እንጀራና ፡ ሁለቱን ፡ ዓሣ ፡ እንዲህ ፡ በማለት ፡ ይፈታዋል ፤ « አምስቱ ፡ ያምስቱ ፡ አዕማደ ፡ ምሥጢር ፤ ሁለቱ ፡ ዓሣ ፡ የፍቅረ ፡ ቢጽና (የባልንጀራ) ፡ የፍቅረ ፡ እግዚአብሔር ›› ምልክት ፡ እንደሆን ፡ ይተነትነዋል ፡፡

ስለዚህ ፡ እነዚህ ፡ ሕዝቦች ፡ ተራራው ፡ ላይ ፡ ከኢየሱስ ፡ ሲያደምጡት ፡ የዋሉት ፡ ስለ ፡ እግዚአብሔር ፡ ፍቅርና ፡ ስለ ፡ ወንድማማችነት ፡ ፍቅር ፡ ነበር ፡ ማለት ፡ ነው ፡፡  ታድያ ፡ በትምህርቱ ፡ ልባቸው ፡ በጣም ፡ ስለተነካ ፡ ወድያውኑ ፡ የለውጥ ፡ ሂደት ፡ ጀመሩ ፡፡ በትምህርቱም ፡ መጨረሻ ፡ ላይ ፡ ሕዝቡ ፡ በረሃብ ፡ ስለተንገላታ  ፡ ምግብ ፡ አስፈለገ ፡፡ ከሕዝቡ ፡ መካከል ፡ ደግሞ ፡ በኢየሱስ ፡ ትምህርት ፡ ልቡ ፡ እጅግ ፡ በጣም ፡ የተነካው ፡ ፈጠን ፡ በማለት ፡ እኔ ፡ ዘንድ ፡ አምስት ፡ እንጀራና ፡ ሁለት ፡ ዓሣዎች ፡ አሉ ፡ በማለት ፡ ለጋራ ፡ አገልግሎት ፡ ሲያበረክት ፡ ሌላውም ፡ ሕዝብ ፡ ራስ ፡ ወዳድነቱን ፡ አሸንፎ ፡ የወንድማማችነትን ፡ ፍቅር ፡ ተላብሶ ፡ ያለውን ፡ በሙሉ ፡ በኢየሱስ ፡ እግር ፡ ሥር ፡ ማኖር ፡ ጀመረ ፡፡ ያኔ ፡ የፍቅር ፡ ሥራ ፡ በሕዝቡ ፡ ዘንድ ፡ ተከናወነ ፡፡ ኢየሱስም ፡ ያንን ፡ ባርኮ ፡ አከፋፈላቸው ፡፡ በዚህ ፡ መልኩ ፡ በፍቅር ፡ ተገፋፍተው ፡ የፍቅርን ፡ ሥራ ፡ ሰርተው ፡ በወንድማማችነት ፡ መንፈስ ፡ በአንድ ፡ ማዕድ ፡ ዙርያ ፡ ተሰባስበው ፡ ያቀረቡትን ፡ ሁሉ ፡ በኢየሱስ ፡ ተባርኮላቸው ፡ ስለበሉ ፡ ከታሰበው ፡ በላይ ፡ የተትረፈረፈ ፡ ምግብ ፡ ሊሰበሰብ ፡ ቻለ ፡ በማለት ፡ ያብራሩታል ፡፡

የእነዚህ ፡ ሊቃውንት ፡ ማብራርያ ፡ ትምህርት ፡ ሰጪነቱና ፡ የታምራቱን ፡ ትርጓሜ ፡ የበለጠ ፡ ለመረዳት ፡ የግንዛቤ ፡ አድማስ ፡ ማስፋቱ ፡ ምንም ፡ አይነት ፡ ጥርጣሬ ፡ የለውም ፡፡ በተለይም ፡ ነገሩን ፡ ከፍቅር ፡ ሥራ ፡ ጋር ፡ በማያያዝ ፡ ማለትም ፡ የኢየሱስን ፡ ቃል ፡ በደንብ ፡ የተረዳ ፡ ሰው ፡ ከእኔነቱ ፡ ወይም ፡ ከራስ ፡ ወዳድነቱን ፡ ወጥቶ ፡ ለሌሎች ፡ በማሰብ ፡ ያለውን ፡ ፍቅርም ፡ ሆነ ፡ ንብረት ፡ ከሌሎች ፡ ጋር ፡ በበጎ ፡ ፈቃደኝነት ፡ ወደ ፡ ማከፋፈል ፡ ውሳኔ ፡ መድረሱ ፡ አንድ ፡ የለውጥ ፡ ሂደት ፡ ብቻ ፡ ሳይሆን ፡ የኢየሱስ ፡ ቃል ፡ በጎ ፡ ፈቃድ ፡ ባላቸው ፡ ሰዎች ፡ ሕይወት ፡ ውስጥ ፡ ገብቶ ፡ ወድያውኑ ፡ ፍሬ ፡ እንደሚያፈራ ፡ የሚያሳይ ፡ ነው ፡፡ ነገር ፡ ግን ፡ ከላይ ፡ ካየናቸው ፡ ማብራሪያዎች ፡ ሁሉ ፡ የትኛው ፡ የተሻለ ፡ ነው ፡ ወይም ፡ የበለጠ ፡ ትርጉም ፡ ያለው ፡ የትኛው ፡ ነው ፡ ወይም ፡ ትክክለኛ ፡ ትርጉሙ ፡ ይህ ፡ ነው ፡ በማለት ፡ መወሰን ፡ ስለማይቻል ፡ እያንዳንዱ ፡ አንባቢ ፡ ለራሱ ፡ መንፈሳዊ ፡ ሕይወት ፡ የበለጠ ፡ ትርጉም ፡ የሚሰጥለትን ፡ የመምረጥ ፡ ባለ ፡ ሙሉ ፡ መብትነቱ ፡ የተረጋገጠ ፡ ነው ፡፡ በእኛ ፡ እይታ ፡ ግን ፡ ዮሐ 6  ፡ እንዳለ ፡ በማንበብ ፡ ከምሥጢረ ፡ ቅ.ቁርባን ፡ ጋር ፡ ያለው ፡ ግኑኝነት ፡ በትኩረት ፡ እንዲታይና ፡ እንድናስተነትንበት ፡ ግብዣችን ፡ ነው ፡፡

ይህንን ፡ ትምህርታችን ፡ የምናጠቃልለው ፡ በዮሐ 6 ፡ 15 ፡ ላይ ፡ በተገለጸው ፡ የምስክርነት ፡ ቃል ፡ ይሆናል ፡፡ ሦስቱም ፡ ወንጌላውያን (ማቴ ፣ ማር እና ሉቃ) ፡ ይህንን ፡ የወንጌል ፡ ክፍል ፡ የሚደመድሙት ፡ ሕዝቡ ፡ በሙሉ ፡ በልተው ፡ እንደጠገቡና ፡ አሥራ ፡ ሁለት ፡ መሶብ ፡ ቀሪ ፡ ምግብ ፡ እንደተሰበሰበ ፡ በመግለጽ ፡ ብቻ ፡ ሲሆን ፡ ቅ.ዮሐንስ ፡ ግን « ሰዎቹም ፡ ኢየሱስ ፡ ያደረገውን ፡ ታምራዊ ፡ ምልክት ፡ ካዩ ፡ በኃላ ፡  ወደ ፡ ዓለም ፡ የሚመጣው ፡ ነብይ ፡ በእርግጥ ፡ ይህ ፡ ነው ›› ብለው ፡ ሲመሰክሩና ፡ ሊያነግሱትም ፡ ፈልገው ፡ እንደነበር ፡ የገልጻል ፡፡ ኢየሱስም ፡ ይህንን ፡ ሀሳባቸውን ፡ ዐውቆ ፡ እንደ ፡ ገና ፡ ብቻውን ፡ ወደ ፡ ተራራ ፡ ገለል ፡ እንዳለ ፡ ቅ. ዮሐንስ ፡ አበክሮ ፡ ይገልጻል ፡፡ በእርግጥም ፡ ቅ.ዮሐንስ ፡ በወንጌሉ ፡ ውስጥ ፡ በተለያየ ፡ ቦታዎች ፡ የምስክርነትን ፡ አስፈላጊነት ፡ አበክሮ ፡ ይገልጻል ፡፡ እንደ ፡ ቅ.ዮሐንስ ፡ አመለካከት ፡ ኢየሱስን ፡ ያገኘ ፣ ከኢየሱስ ፡ የተወሰነ ፡ ጊዜ ፡ እንኳን ፡ የሳለፈ ፣ በኢየሱስ ፡ የተፈወሰ ፣ በኢየሱስ ፡ ከጨለማ ፡ ወደ ፡ ብርሃን ፡ የተሸጋገረ ፣ በአጠቃላይ ፡ በኢየሱስ ፡ ሕይወቱን ፡ የተቀየረ ፡ ዝም ፡ አይልም ፤ ማለትም ፡ አይችልም ፤ ፍቅሩ ፡ ግድ ፡ ይለዋልና ፡ ፍርሃትንና ፡ ይሉኝታን ፡ አውልቆ ፡ በመጣል ፡ ያመሰግናል ፣ ይመሰክራል ፣ የተደረገለትንም ፡ ይተርካል ፣ ለሌሎችም ፡ አንተም ፡ ናና ፡ እይ ፡ በማለት ፡ መንገዱን ፡ ያሳያል ፡፡ ለምሳሌ ፡ ፊልጶስ ፡ ኢየሱስን ፡ ካገኘው ፡ በኋላ ፡ ለናትናኤል « መጥተህ ፡ እይ ›› አለው ፡፡ ሳምራዊቷም « እንስራዋን ፡ ትታ ፡ ወደ ፡ ከተማ ፡ ተመለሰች ፤ ለሕዝቡም ፡ ያደረግሁትን ፡ ሁሉ ፡ የነገረኝን ፡ ኑና ፡ እዩ ፤ እርሱ ፡ ክርስቶስ ፡ ይሆን ፡ እንዴ ?›› እያለች ፡ መሰከረች (ዮሐ 4 ፡ 28) ፡፡ ዐይነ ፡ ስውር ፡ ሆኖ ፡ የተወለደውን ፡ ሰው ፡ በኢየሱስ ፡ ከተፈወሰ ፡ በኋላ ፡ ፈሪሳውያን ፡ ይዘውት « ዐይንህን ፡ ስለ ፡ ከፈተው ፡ ሰው ፡ እንግዲህ ፡ አንተ ፡ ምን ፡ ትላለህ ?›› ሲሉት ፡ በድፍረት ፡ አጥማጆቹን ፡ ፈሪሳውያንን ፡ ቅንጣት ፡ እንኳ ፡ ሳይፈራ « እርሱ ፡ ነብይ ፡ ነው ፡ እናንተም ፡ ደቀ ፡ መዛሙርቱ ፡ ልትሆኑ ፡ ተሻላችሁ ? ›› በማለት ፡ ነው ፡ ምስክርነቱን ፡ በመግለጽ ፡ ያፋጠጣቸው (ዮሐ 9 ፡ 26-28) ፡፡ ስለዚህ ፡ ቅ.ዮሐንስ ፡ ለእያንዳንዳችን ፡ በእለታዊ ፡ ሕይወታችን ፡ ውስጥ ፡ ስለ ፡ እምነታችንና ፡ ስላመነው ፡ ማንነት ፡ በየትኛውም ፡ ቦታም ፡ ሆነ ፡ በየትኛውም ፡ ሁኔታ ፡ ውስጥ ፡ ምንም ፡ ሳንፈራና ፡ ሳናፍር ፡ እንድንመሰክር ፡ ጥሪውን ፡ ያስተላልፍልናል ፡፡

አይሁዳውያን ፡ ኢየሱስን ፡ ሊያነግሡት ፡ የፈለጉት ፡ በእርግጥ ፡ በልተው ፡ ስለጠገቡና ፡ ሌሎችም ፡ ታምራቶች ፡ ስላዩ ፡ ነው ፡፡ አንድምታ ዮሐ 6 ፡ 15 ፡ እንደሚለው « ቢራቡ ፡ ያመሳል ፣ ቢታመሙ ፡ ይፈውሳል ፣ ቢሞቱ ፡ ያስነሣልና ፡ እንዲህ ፡ ያለውን ፡ ቢያነግሡት ፡ እንደወደዱ ፡ አውቆባቸው ፡ ለብቻው ፡ ወደ ፡ ተራራ ፡ ሄደ ›› ይላል ፡፡ ስለዚህ ፡ የምናመሰግነው ፡ ወይም ፡ የምንመሰክረው ፡ አንድ ፡ ጥቅም ፡ ስላገኘን ፡ ወይም ፡ ስለተደረገልን ፡ ነገር ፡ ብቻ ፡ ሳይሆን ፡ የሕይወታችን ፡ ሁሉ ፡ መሠረት ፡ ከመሆኑም ፡ አልፎ ፡ ያለ ፡ እርሱ ፡ መኖር ፡ የማንችል ፡ ወይም ፡ እኛነታችን ፡ ሁሉ ፡ የታነጸው ፡ በእርሱ ፡ መሆኑን ፡ አውቀን « ቢመችም ፡ ባይመችም ›› እንደሚለው ፡ ሐ. ጳውሎስ ፡ ሁሌም ፡ ለማመስገንና ፡ ለመመስከር ፡ ታጥቀን ፡ ዝግጁዎች ፡ በመሆን ፡ እንቁም ፡፡ ለዚሁም ፡ እግዚአብሔር ፡ እራሱ ፡ ይርዳን ፡ አሜን ፡፡

ከአባ ፡ ምሥራቅ ፡ ጥዩ

ከእምድብር ፡ ሀገረስብከት

አድራሻችን

logo

                 ገዳመ ቅዱስ ዮሴፍ ዘሲታውያን

                    ፖ.ሳ.ቁ. 21902
                 አዲስ አበባ - ኢትዮጵያ
             Phone: +251 (116) 461-435

              Fax +251 (116) 458-988

               contact@ethiocist.org

             https://www.ethiocist.org

 
 

ለድረ ገጻችን የሚሆን ጽሑፍ ካለዎ

1- የኢሜል አድራሻችንን webpageorganizers@gmail.comን ተጠቅመው አሊያም

2- ይህን ሲጫኑ በሚያገኙት CONTACT FORMበሚለው ቅጽ ላይ ጽሑፍዎን ለጥፈው ወይም 

3-facebook አድራሻችን https://www.facebook.com/ethiocist.org በግል መልእከት ይላኩልን

በተጨማሪም የሚያካፍሉት ጠቃሚ የድረገጽ አድራሻ ካለዎ ይላኩልን።   

መልእክት ከር.ሊ.ጳ. ፍራንቼስኮስ

pope"ይቅርታን እና ምሕረትን ማድረግ የሰላማዊ ሕይወት መሠረት ነው"።

“ይቅር ማለት እና ምህረትን ማድረግ የሕይወት ዘይቤያችን ቢሆኑ ኖሮ፥ ስንት ጦርነት፣ ስቃይ እና መከራን እናስቀር ነበር! በግንኙነቶቻችን ሁሉ ይቅርታን የሚያደርግ ፍቅር ያስፈልጋል። ይኸውም በባል እና ሚስት፤ በወላጆች እና በልጆች መካከል እንዲሁም በአካባቢያችን፣ በማኅበረሰባችን እና በፖለቲካውም ማለት ነው። እንዲሁም ይቅርታን ለማድረግ ጥረት የማናደርግ ከሆነ፥ ይቅር አይባልልንም” ማለታቸው ተገልጿል።

ምንጭ - ቫቲካን ራድዮ አማርኛ ዝግጅት