፫ - “ፈቃድህ በሰማይ እንደሆነች እንዲሁም በምድር ትሁን”
- Category: በሰማያት የምትኖር አባታችን ሆይ ጸሎት ሰባት ልመናዎች
- Published: Thursday, 13 October 2011 19:11
- Written by Super User
- Hits: 4302
- 13 Oct
፫ - “ፈቃድህ በሰማይ እንደሆነች እንዲሁም በምድር ትሁን”
አባታችን “ሰዎች ሁሉ እንዲድኑና እውነቱን እንዲያውቁ ይወዳል፡፡” እርሱ “ማንም እንደይጠፋ ወዶ ስለ እናንተ ይታገሣል፡፡” ትዕዛዙም “እርስ በርሳችሁ ትዋደዱ ዘንድ፣ እንደወደድኋችሁ እናንተ ደግሞ እርስ በርሳችሁ ተዋደዱ” የሚል ነው፡፡ ይህ ትእዛዝ ሌሎቹን ትእዛዛት ሁሉ የሚያጠቃልልና የኢየሱስንም ፈቃድ የሚገልጽ ነው፡፡
በክርስቶስ ለማድረግ እንደ ወደደ እንደ አሳቡ የፈቃድን ምስጢር አስታውቆናልና፤ በዘመን ፍጻሜ ይደረግ ዘንድ ያለው አሳቡም በሰማይና በምድር ያለውን ሁሉ በክርስቶስ ለመጠቅለል ነው፡፡ እንደ ፈቃዱ ምክር ሁሉን የሚሠራ እንደ እርሱ አሳብ አስቀድመን የተወሰንን በክርስቶስ ደግሞ ርስትን ተቀበልን፡፡ ይህን የፍቅር እቅድ በሰማይ እንደሆነው ሁሉ እንዲሁ በምድርም ላይ ሙሉ በሙሉ እውን ይሆን ዘንድ እንለምናለን፡፡
የአብ ፈቃድ በማያዳግም ሁኔታ ሙሉ ፍጻሜ ያገኘው በክርስቶስና በእርሱ ሰብአዊ ፍቃድ ነው፡፡ ኢየሱስ ወደዚህ ዓለም ሲመጣ “አምላኬ ሆይ፣ … እነሆ ፈቃድህን ለመፈጸም መጥቻለሁ” አለ፡፡ “እኔ ደስ የሚያሰኘውን ዘወትር አደርጋለሁ” ማለት የሚችለው ኢየሱስ ብቻ ነው፡፡ በስቃዩ ጊዜ ሲጸልይ ይህን ፈቃድ ሙሉ በሙሉ ይቀበላል፡፡ “የእኔ ፈቃድ አይሁን ያንተ እንጂ” ሲልም ይናገራል፡፡ በዚህም የተነሳ ኢየሱስ “ክፉ ከሆነ ከአሁኑ ዓለም ያድነን ዘንድ እንደ አምላካችንና እንደ አባታችን ፈቃድ ስለኃጢአታችን ራሱን ሰጠ” “በዚህም ፈቃድ የኢየሱስ ክርስቶስን ሥጋ አንድ ጊዜ ፈጽሞ በማቅረብ ተቀድሰናል፡፡
“ኢየሱስ ምንም እንኳ ልጅ ቢሆንም ከተቀበለው መከራ መታዘዝን ተማረ፡፡” በእርሱ ልጅነትን ያገኘን እኛ ኃጢአተኞች ፍጡራን መታዘዝን እንማር ዘንድ ምን ያህል ዕውቀት አለን! የአባታችን የእግዚአብሔርን ፈቃድና እርሱ ስለዓለም ሕይወት ያለው የድኀነት እቅድ እንዲፈጸም ፈቃዳችንን ከልጁ ፈቃድ ጋር ያዋሕድልን ዘንድ እንለምነዋለን፡፡ እኛ ይህን የማድረግ ችሎታ ፈጽሞ የለንም፤ ይሁን እንጂ ራሳችንን ከክርስቶስና ከእርሱም መንፈስ ቅዱስ ኃይል ጋር ካዋሐድን ፈቃዳችንን ለአብ ማስገዛት እንዲሁም ልጁ ሁልጊዜ የሚመርጠውን ነገር ለመምረጥ- አብን ደስ የሚያሰኝ ነገር ለመፈጸም መወሰን እንችላለን፡፡
ራሳችንን ሙሉ በሙሉ ለክርስቶስ በመስጠት ከእርሱ ጋር አንድ መንፈስ መሆን ስለምንችል፤ በሰማይ እንደሆነ ሁሉ በምድርም ፍጹም ይሆን ዘንድ ፈቃዱን እንፈጽማለን፡፡
ትሑታን እንሆን ዘንድ ኢየሱስ ክርስቶስ እንዴት እንደሚያስተምረን አስቡ፡፡ መልካም ተግባራችን ፍሬያማ የሚሆነው ብቻ ሳይሆን ከእግዚአብሔር በሚሰጠን ጸጋ መሆኑን እንድንገነዘብ በማድረግ ነው፡፡ አምላክ እያንዳንዱ ምእመን በአጠቃላይ ለመላው ዓለም እንዲጸልይ ያዝዛል፡፡ እርሱ “ፈቃድህ በእኔ ወይም በእኛ ይሁን” አላለም፤ ነገር ግን “በምድር ላይ ይሁን” አለ እንጂ፡፡ እንደዚህ ያለበትም ምክንያት፣ ስሕተት በምድር ፈጽሞ እንዲጠፋ፤ እውነት በምድር ላይ ሥር እንዲሰድድ፣ ክፋት በምድር እንደወገድ፣ መልካም ምግባር በምድር እንዲያብብ፣ ምድርም ከሰማይ በምንም ዓይነት የተለየች እንዳትሆን ነው፡፡
በጸሎት “የእግዚአብሔር ፈቃድ” ለይተን ማወቅን እርሱንም የምንፈጽምበት ጽናት ማግኘት እንችላለን፡፡ ኢየሱስ ሰው ወደ መንግሥተ ሰማያት የሚባው ቃላትን በመናገር ሳይሆን “በሰማያት ያለውን የአባቴን ፈቃድ በመፈጸም” እንደሆነ ያስተምረናል፡፡
“እግዚአብሔርን የሚፈራ ፈቃዱንም የሚያደርግ ብኖር ያንን እግዚአብሔር ይሰማዋል፡፡” ከሁሉም በላይ በመሥዋዕተ ቅዳሴ የሚገለጸው፣ ቤተ ክርስቲያን በጌታዋ ስም የምታቀርበው ጸሎት ኃይል ይህን ይመስላል፡፡ የቤተ ክርስቲያን ጸሎት ፍፁም ቅድስት ከሆነችው እመአምላክና ፍላጐታቸውን ፈቃዱን ብቻ መፈጸም በመሆኑ ጌታን ደስ ከሚያሰኙት ቅዱሳን ጋር የሚደረግ የምልጃ ሱታፌ ነው፡፡
“ፈቃድህ በሰማይ እንደሆነች እንዲሁም በምድር ትሁን” የሚሉትን ቃላት “በጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በራሱ እንደሆነው በቤተ ክርስቲያንም ይሁን” ወይም “የአባቱን ፈቃድ እንደፈጸመው ሙሽራ ሁሉ ለእርሱ በታጨችው ሙሽራይቱም ይሁን የሚያሰሙ አድርጐ መውሰድ ከእውነቱ ጋር የሚጣረዝ አይሆንም፡፡
/የካቶሊክ ቤተክርስቲያን ትምህርተ ክርስቶስ ከቁጥር 2822-2827/