-
Category: ቅዱስ ቁርባን
-
Published: Friday, 06 November 2015 22:01
-
Written by Super User
-
Hits: 7406
-
Print
-
Email
-
06 Nov
“ቅዱስ ቁርባን ቤተክርስቲያንን ይሠራል፤ ያንጻል፤ ቤ/ያን ደግሞ ቅ. ቁርባንን ትሠራለች” ካርዲናል ሄንሪ ዴ ሉባክ - ኢየሱሳዊ /1896-1991/
አንዳንድ ጊዜ ቤተ ክርስቲያንን እንደ ሰው ሠራሽ ተቋም ብቻ የሚያስቡ ሰዎች “ክርስቶስ እምነትን፣ ሕይወትን እንጂ ሃይማኖትን/ቤተክርስቲያንን/የእምነት ተቋምን አላመጣም” እና መሰል ዓረፍተ ነገሮችን ሲናገሩ ይደመጣሉ። በርግጥ እንደነዚህ ዓይነት ሰዎች ይህን ለማለት እውነተኛ ምክንያታቸው ምን እንደሆነ ባናውቅም ስለራሳችን እምነት ካወራን ግን ኢየሱስ በተደራጁ ሰዎች (በሐዋርያት፣ በደቀመዛሙርት፣ በአርድእት...) መካከል እንደነበርና በዚያ መልኩም ይቀጥሉ ዘንድ እንዳዘዛቸውእናነባለን። ለምሣሌም በዮሐ 21፡15-17 ላይ ስምዖን ጴጥሮስን ክርስቶስ ግልገሎቹን፣ ጠቦቶቹንና በጎቹን እንዲያሰማራና እንዲጠብቅ አደራ እንደሰጠው ፤ እንዲሁም በማቴ 16፡18-19 ላይም «18 እኔም እልሃለሁ፥ አንተ ጴጥሮስ ነህ፥ በዚችም ዓለት ላይ ቤተ ክርስቲያኔን እሠራለሁ፥ የገሃነም ደጆችም አይችሉአትም።19 የመንግሥተ ሰማያትንም መክፈቻዎች እሰጥሃለሁ፤ በምድር የምታስረው ሁሉ በሰማያት የታሰረ ይሆናል፥ በምድርም የምትፈታው ሁሉ በሰማያት የተፈታ ይሆናል።» ማለቱን ልብ ይሏል።
ሐዋርያቱም የዚህን አደራ ኀላፊነት ለመወጣት ሲሰባሰቡና ሲጸልዩ፤ ወሳኝ የእምነት አንቀጾችን ሲወስኑ፤ ከጌታ የተቀበሉትን አገልግሎታቸውን እነርሱም ለቀጣይ ትውልድ በአደራ ሲያስተላልፉና መሰል ትውፊቶችን አክብረው ሲያስከብሩ በሐዋርያት ሥራ እና በተለያዩ የአዲስ ኪዳን መልእክቶቻቸው ውስጥ እናነባለን። በርግጥ ክርስቶስ በአካል ከሰዎች ጋር ኑሮ እንዴት መኖር እንደሚገባ ኖሮ ያሳየ ፍጹም አምላክና ፍጹም ሰው እንጂ መንፈስ ብቻ ወይም የሆነ የአእምሮ ውልብታ ምትሐት አይደለም።
ይህንን እውነት ስንናገር በወንጌል ጊዜና በሐዋርያት ጊዜ ብቻ እንዲህ ነበር ለማለት አይደለም፤ ምክንያቱም ክርስቶስ በስሙ በሚሰበሰቡ ሰዎች መካከል ይገኛል «ሁለት ወይም ሦስት በስሜ በሚሰበሰቡበት በዚያ በመካከላቸው እሆናለሁና።» ማቴ 18፡20። ቤተ ክርስቲያናችን ይህን መገኘት በብዙ መልኩ ታስተምራለች። ከእነዚህም መገኘቶች መካከል ደግሞ ክርስቲያናዊ መሠረት አድርጋ የክርስቶስን በቅ. ቁርባን መገኘት ታስተምራለች፤ ምክንያቱም እሱ ራሱ ለዘለዓለማዊነታችን አንድ ዋስትናን ያደረገልን፣ በምንም መልኩ ሊቀየርና ሊደራደር የማይችለው ቅ. ቁርባን በመሆኑ ነው (ዮሐ 6)። እንደ ቤ/ያናችን እምነት ቤ/ያን በክርስቶስ ዙሪያ የሚሰባሰቡ የአማኞች ስብስብ ነው። ከዚህም እውነት የተነሣ “ቅዱስ ቁርባን ቤተክርስቲያንን ይሠራል” የሚለው ሃሳብ ግልጽ ነው። በክርስቶስ ሥጋና ደም ዙሪያ የእርሱ የሆኑት ይሰበሰባሉ፤ ያም የክርስቶሳውያን ስብስብ ናቸው።
በሌላ መልኩ ደግሞ እነዚህ በሥጋውና ደሙ ዙሪያ የሚሰበሰቡ ሰዎች ወይም ቅ. ቁርባንን የሚቀበሉ ሰዎች ኃይል ያለውን አካል ይቀበላሉና ወደ ክርስቶስ ወገንነት ይለወጣሉ፤ የክርስቶስ ፈቃድና ሕይወትን ይማራሉ፤ ከቃል በላይ የሆነውን ትስስርና ቅርበት ይቀምሳሉ። ቅዱስ ሥጋውና ደሙ ከአካላቸው ጋር በመዋሐድ ነፍሳቸውን ለበለጠ ፍጽምና ያነሣሣል፤ ይህን መሰል ሕይወትም እንዲቀጥል ቅ. ቁርባንን ዘወትር ይናፍቃሉ፤ ይሰባሰባሉ፤ ለቅ. ቁርባን መገኘት ራሳቸውን ያስገዛሉ። የሁለተኛው ቫቲካን ሰነድ “በቅ. ቁርባን ኅብስት የክርስቲያኖች አንድነት እውን ይሆናል፤ እነርሱም ከክርስቶስ አካል ጋር አንድ ይሆናሉ” ይላል /LG, ስለቤ/ያን ቀኖናዊ አቋም ቁ.3/። ይህም 1ቆሮ 10፡16-17ን ያንፀባርቃል፡- «የምንባርከው የበረከት ጽዋ ከክርስቶስ ደም ጋር ኅብረት ያለው አይደለምን? የምንቆርሰውስ እንጀራ ከክርስቶስ ሥጋ ጋር ኅብረት ያለው አይደለምን? 17 አንድ እንጀራ ስለ ሆነ፥ እኛ ብዙዎች ስንሆን አንድ ሥጋ ነን፤ ሁላችን ያን አንዱን እንጀራ እንካፈላለንና።»
ቅ. ቁርባን ቤ/ያንን ይሠራል ሲባል የክርስቶስ ህላዌ ክርስቲያኖችን የአካሉ ክፍል ያደርጋቸዋል ማለት ነው፤ ይህንን እውነት ማወቅ በራሱ በቤ/ያን ስም የሚከሠቱ ስህተቶችን እንድናስወግድ ያግዘናል። የአምልኮ ሥርዓታችን ምንጭና ግብ በቀራንዮ በመስቀል፣ በቅዱስ ቁርባን ዛሬም ራሱን የሰጠን ጌታ ነው። መጸለያችንና መሰባሰባችን በርሱና ለርሱ ትኩረትን በሰጠ ሁኔታ ነው። የመሰባሰባችን ግብም በቅዱስ ቁርባን ራሱን የሰጠንን ጌታ ለማምለክና በሕይወታችን ለማክበር ነው።
ቤ/ያን መቼውንም ቢሆን ከክርስቶስ ውጪ የእገሌ መሆን አትችልም፤ መሥራቿ፣ ማእከሏም ሆነ መድረሻዋ ራሱ ክርስቶስ ነው። ቅ. ጳውሎስ ይህን ትምህርት ጎላ በማድረግ ከሰዎች ጋር የተጣበቁ «ክርስቲያኖችን» እንዲላቀቁ ይገስፃቸዋል። ሰው የመከተል አባዜ ለተጠናወታቸው የቆሮንጦስ ክርስቲያኖች እውነቱን ለመናገር ምንም ያህል ጊዜ አላባከነም በመጀመሪያ መልእክቱ 1፡10-17 ላይ እንዲህ ይላቸዋል፤
«10 ነገር ግን፥ ወንድሞች ሆይ፥ ሁላችሁ አንድ ንግግር እንድትናገሩ በአንድ ልብና በአንድ አሳብም የተባበራችሁ እንድትሆኑ እንጂ መለያየት በመካከላችሁ እንዳይሆን በጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስ ስም እለምናችኋለሁ። 11 ወንድሞቼ ሆይ፥ በመካከላችሁ ክርክር እንዳለ ስለ እናንተ የቀሎዔ ቤተ ሰዎች አስታውቀውኛልና። 12 ይህንም እላለሁ። እያንዳንዳችሁ። እኔ የጳውሎስ ነኝ፥ እኔስ የአጵሎስ ነኝ፥ እኔ ግን የኬፋ ነኝ፥ እኔስ የክርስቶስ ነኝ ትላላችሁ። 13 ክርስቶስ ተከፍሎአልን? ጳውሎስስ ስለ እናንተ ተሰቀለን? ወይስ በጳውሎስ ስም ተጠመቃችሁን? 14-15 በስሜ እንደ ተጠመቃችሁ ማንም እንዳይል ከቀርስጶስና ከጋይዮስ በቀር ከእናንተ አንድን እንኳ ስላላጠመቅሁ እግዚአብሔርን አመሰግናለሁ። 16 የእስጢፋኖስንም ቤተ ሰዎች ደግሞ አጥምቄአለሁ፤ ጨምሬ ሌላ አጥምቄ እንደ ሆነ አላውቅም። 17 ለማጥመቅ ክርስቶስ አልላከኝምና፥ ወንጌልን ልሰብክ እንጂ፤ የክርስቶስ መስቀል ከንቱ እንዳይሆን በቃል ጥበብ አይደለም።»
እርሱ እንደተረዳው ከሆነ የቆሮንጦሷ ቤ/ያን የመከፋፈል ስጋት ከትምህርት ወይም ከሥርዓት ሐቀኛነት የተነሣ ሳይሆን የተለያዩ የቤ/ያን መሪዎች ጋር የመጣበቅ ዝንባሌ ያመጣው ነበር፤ ልክ ሐዋርያት በክርስቶስ ማንነት ተማርከው እንደተከተሉት ሁሉ አንዳንድ ክርስቲያኖችም ወደ ክርስቶስ ሊመሩ በሚገባቸው ሰዎች ብቻ ራሳቸውን ገድበው ወደ ክርስቶስ መዝለቁ ያዳግታቸዋል።
አጵሎስ በሐሥ 18፡24-28 ላይ የዮሐንስ መጥምቅ ተከታይ የነበረ መጽሐፍ ቅዱስን ጠንቅቆ የተማረና ጥሩ የመናገር ችሎታ ያለው አይሁድ መሆኑ ተጠቅሷል፤ በተጨማሪም ስለጌታ በመንፈስ የተቃጠለ ሆኖ በትክክል የሚሰብክና የሚያስተምር ነበር። ጵርስቅላና አቂላ ይበልጥ ወደ ክርስቲያናዊው መንገድ እንዲገባ አስተምረውት የቆሮንጦስ ቤ/ያንን ተቀላቅሏል። «ኬፋ» የተሰኘውም ጴጥሮስ፣ ስምዖን የዮና ልጅም ተብሎ የተጠራው ነው። ኬፋ የሚለው የአረማይስጥ ቃል ክርስቶስ ስምዖንን «ዓለት» «ጴጥሮስ» የሚለውን ትርጓሜ ለመስጠት የተጠቀመበት ስም ነው (ማቴ 16፡18)። ቅዱስ ጴጥሮስ በቆሮንጦስ አገልግሎ ባይሆንም ወይም እርሱ ከሰበከበት የመጡ ክርስቲያኖች በዚያ የሚገኙ ስለሆነ ቢሆንም ምናልባት ቅ. ጳውሎስ የኬፋን ስም የሚጠቅሰው የአማኞቹን እይታ ለማስፋት እንዲያግዝ ብሎ ይሆናል። ስለዚህ እንደ ሰው እይታ ከሆነ እነዚህ መሪዎች ሰው በቀላሉ ይከተላቸው ዘንድ የሚያበቃ ሰዋዊ መስፈርት ነበራቸው፤ ራሱ ቅዱስ ጳውሎስም ቢሆን በትምህርቱም ሆነ በሌሎች ብቃቱ ሰዎች ሊያነጻጽሩት የሚችል ዓይነት ሰው ነበር፤ ሆኖም ግን ይህ ዓይነት አካሄድ የክርስቶስ አካል የሆነችውን ቤተ ክርስቲያንን የሚያሰቃይ መሆኑን ጠንቅቆ ያውቃል፤ እንደ አንድ አካል የምትቆጠረው ቤተ ክርስቲያን አንድ ራስ ብቻ ይኖራት ዘንድ አግባብ ነው።
1ቆሮ 3፡1-9/4፡6-7 ላይ ለቆሮንጦስ ቤ/ያን የመከፋፈልን ጉዳት ያደረሰው የጳውሎስና አጵሎስ መሆኑ ግልፅ ነው። «1 እኔም፥ ወንድሞች ሆይ፥ የሥጋ እንደ መሆናችሁ፥ በክርስቶስም ሕፃናት እንደ መሆናችሁ እንጂ መንፈሳውያን እንደ መሆናችሁ ልናገራችሁ አልቻልሁም። 2 ገና ጽኑ መብል ለመብላት አትችሉም ነበርና ወተት ጋትኋችሁ፤ 3 ገና ሥጋውያን ናችሁና እስከ አሁን ድረስ ገና አትችሉም። ቅናትና ክርክር ስለሚገኝባችሁ ሥጋውያን መሆናችሁ አይደላችሁምን? እንደ ሰው ልማድስ አትመላለሱምን? 4 አንዱ። እኔ የጳውሎስ ነኝ፥ ሁለተኛውም። እኔ የአጵሎስ ነኝ ቢል ሰዎች ብቻ መሆናችሁ አይደለምን? 5 አጵሎስ እንግዲህ ምንድር ነው? ጳውሎስስ ምንድር ነው? በእነርሱ እጅ ያመናችሁ አገልጋዮች ናቸው፤ ለእያንዳንዳቸውም ጌታ እንደ ሰጣቸው ያገለግላሉ። 6 እኔ ተከልሁ አጵሎስም አጠጣ ነገር ግን እግዚአብሔር ያሳድግ ነበር፤ 7 እንግዲያስ የሚያሳድግ እግዚአብሔር እንጂ የሚተክል ቢሆን ወይም የሚያጠጣ ቢሆን አንዳች አይደለም። 8 የሚተክልና የሚያጠጣ አንድ ናቸው፥ ነገር ግን እያንዳንዱ እንደ ራሱ ድካም መጠን የራሱን ደመወዝ ይቀበላል። 9 የእግዚአብሔር እርሻ ናችሁ፤ የእግዚአብሔር ሕንፃ ናችሁ፤ ከእርሱ ጋር አብረን የምንሠራ ነንና።» ጳውሎስ እዚህ ላይ በክርስቶስ ሳይሆን በአገልጋዮች ላይ ትኩረታቸውን ያደረጉ ሰዎችን እንደ ሕፃናት እንጂ እንደ መንፈሳውያን ለማየት እንደሚቸገር ገልጿል፤ ቅ. ቁርባን የቤ/ያን ማእከል መሆኑን ማስተዋል ከዚህ ስህተት ይታደገናል። በተመሳሳይ ሁኔታም በክርስቶስ አገልጋይነት ስም ራሳቸው ላይ የስምና የቅጽል ብዛት ለሚከምሩት እንዲህ ይላል፡- 4፡6-7 «6 ወንድሞች ሆይ፥ ስለ አንዱ በአንዱ ላይ አንዳችሁም እንዳይታበዩ። ከተጻፈው አትለፍ የሚለውን በእኛ ትማሩ ዘንድ፥ ይህን በእናንተ ምክንያት ስለ ራሴና ስለ አጵሎስ እንደ ምሳሌ ተናገርሁ። 7 አንተ እንድትበልጥ ማን አድርጎሃል? ያልተቀበልኸውስ ምን አለህ? የተቀበልህ ከሆንህ ግን እንዳልተቀበልህ የምትመካ ስለ ምንድር ነው?» በዚህ መልኩ ሰዎች በእግዚአብሔር ስም በእነርሱ በኩል አንዳች ቢከናወን ምንጩ እግዚአብሔር መሆኑን መዘንጋት እንደሌለባቸው ያስተምራል፤ ከምንጭነቱም ባሻገር ክብሩ ሁሉም ወደ አንድ ግብ ማለትም ወደ እግዚአብሔር መቃኘት እንዳለበት ያሳያል፤ ለዚህም ነው ቅ. ቁርባን የነገሮቻችን ምንጭና ቁንጮ መሆኑን መዘንጋት የሌለብን።
ቅ. ጳውሎስ ሰው ዓይኑን ከክርስቶስ አንስቶ በሰው ላይ ማድረግ ከጀመረ «ክርስቲያን» ወይም የክርስቶስ ተከታይ ተብሎ መጠራቱ የማይስማማ መሆኑ ገብቶታል። በዚያው መልእክቱ 1፡12 ላይ የተጠቀሰው «እኔስ የክርስቶስ ነኝ ትላላችሁ» የሚለው አባባል ለማለት ብቻ እንደሚሉት እንጂ ሰው ላይ ማተኮራቸውን ለመግለፅ የተጠቀመበት ነው። ቅ. ቁርባንን መሠረት፣ ማእከልና መድረሻ አደረግን ማለት ሙላት እንጂ መጉደል እንዳልሆነ በጳውሎስ ንግግር ውስጥ ማየት እንችላለን «ማንም በሰው አይመካ። ነገር ሁሉ የእናንተ ነውና፤ 22 ጳውሎስ ቢሆን አጵሎስም ቢሆን ኬፋም ቢሆን ዓለምም ቢሆን ሕይወትም ቢሆን ሞትም ቢሆን ያለውም ቢሆን የሚመጣውም ቢሆን፥23 ሁሉ የእናንተ ነው፥ እናንተም የክርስቶስ ናችሁ ክርስቶስም የእግዚአብሔር ነው» 1ቆሮ 3፡21-23።
-
Category: ቅዱስ ቁርባን
-
Published: Tuesday, 01 September 2015 09:03
-
Written by Super User
-
Hits: 7329
-
Print
-
Email
-
01 Sep
መሳጭ የቅዱስ ቁርባን ታሪኮች
ቅዱስ ቁርባናዊ ሴቶችና ቅ.ቁርባን በሶቪየት ኅብረት የአፈና ዘመን
(Dominus Est ከሚል በረዳት ጳጳስ አታናሲየስ ሽኔይደር መጽሐፍ የተወሰደ)
ከ1917-1990 ዓ.ም. ድረስ የቆየው የሶቪየት ኅብረት ኮሚኒስታዊ አገዛዝ በምድር ላይ ገነትን መመሥረት የሚመስል ሃሳብ ነበረው። ሆኖም ግን ይህ አገዛዝ በውሸት ላይ፣ በሰብአዊ ክብር ጥሰት፣ እግዚአብሔርንና ቤተ ክርስቲያኑን በመካድና ብሎም በመጥላት ላይ የተመሠረተ ነበርና ብዙም ሊዘልቅ አልቻለም። በዚህ አገዛዝ ሥር ምንም ዓይነት መንፈሳዊ እሴቶች ቦታ ሊኖራቸው አይችልም፣ አልቻለምም ነበር። ሰውን ስለ እግዚአብሔር ህላዌ፣ ስለ ክርስቶስ፣ ስለ ቤተ ክርስቲያን የሚያስታውሱ ነገሮች ሁሉ ከሕዝቡ ሕይወት እንዲጠፋና ከሰዎች እይታ እንዲርቅ ተደርጎ ነበር። ቢሆንም ግን ሰዎችን ስለ እግዚአብሔር መኖር የሚያስታውስ እውነታ ነበር፤ ይህም የካህን መኖር ነበር። ሰዎች ካህንን ሲያዩ የእግዚአብሔርን ህላዌ ሊያስታውሱ ግድ ነበርና እግዚአብሔር የሚለውን ሃሳብ ከሰዎች ለመፋቅ ካህንም ለሰዎች መታየት የለበትም፣ ከመኖር መወገድ አለበት።
የክርስቶስና የቤተ ክርስቲያን አሳዳጆች በውስጣቸው ካህን ብቻ እግዚአብሔርን ለሰዎች መስጠት እንደሚችል፣ ክርስቶስን በቀጥታና በተጨባጭ መልኩ ማለትም በቅዱስ ቁርባን ለሰዎች መስጠቱን ስለሚያውቁ ካህንን ከሁሉ የበለጠ አደገኛ ሰው አድርገው ይቆጥሩት ነበር። በዚህ ምክንያት መሥዋዕተ ቅዳሴን መቀደስ ክልክል ነበር። ይህ ሁሉ ቢደረግም ቅሉ፣ በቤተ ክርስቲያን በተለይም ደግሞ በምሥጢራት በኩል በሥራ ላይ የነበረውን መለኮታዊ ኃይል ማንኛውም ዓይነት የሰው ኃይል ሊያስቀረው አልቻለም።
በነዚያ ጨለማ ዓመታት በሰፊው የሶቪየት ኅብረት ግዛት ቤተ ክርስቲያን በድብቅ ውስጥ ውስጡን መኖርን ተገድዳ ነበር፤ ምንም እንኳ ሊታዩ የሚችሉ ገሃዳዊ መዋቅርና ሕንጻዎች ባይኖሯትም፣ እጅግ ከፍተኛ የሆነ የአገልጋይ ካህናት ቁጥር እጥረት ቢኖርም ወሳኝ ነገሩ ግን ቤ/ያን ሕያው ነበረች፣ እንደውም እጅጉን ሕያው ነበረች። ቤ/ያን እንዲህ ሕያው የሆነችው ቅዱስ ቅርባንን በቋሚነት አላጣችም ነበር፤ ምንም እንኳ ምእመናን ብዙ ጊዜ የመቁረብ እድል ባይኖራቸውም በምሥጢረ ቅዱስ ቁርባን ላይ የተደላደለ እምነት ያላቸውን ምእመናን ቤ/ያን አላጣችም ነበር፤ ባብዛኛው እናቶችና አያቶች የነበሩ በክህነታዊ እምነት ነፍሳቸው የታነጸች ቅ. ቀርባንን ከጥቃትና ከመጥፋት የሚከላከሉ እንዲሁም ላቅ ባለ ፍቅር፣ ክብርና በሚቻላቸው ሁሉ ተገቢውን ጥንቃቄ በማድረግ፤ በመጀመሪያው ክፍለ ዘመን የክርስቲያኖች መንፈስ የተሞሉና «በፍቅርና በፍርሃት» ቅዱስ ቁርባንን ለሌሎች የሚያድሉ አማኝ ሴቶችን ቤ/ያን አላጣችም ነበር።
በጊዜው በሶቪየት ኅብረት ድብቋ ቤ/ያን ውስጥ ከነበሩት ብዙ ተምሳሌውያት ሴትች ቅዱስ ቁርባናዊ ሴቶች መካከል የሦስቱን ሕይወት እናያለን። እነርሱም ማሪያ ሽኔይደር፣ ፑልኬሪያ ኮችና ማሪያ ስታንግ ይባላሉ።
ከሁለተኛው የዓለም ጦርነት በኋላ የስታሊን አገዛዝ ብዙ ጀርመናውያንን ለጉልበት ሥራ በማለት ጥቁር ባሕር ከሚባለው አካባቢ ወደ ቮልጋ ወንዝ አጋዛቸው። ከከተማ በተገለለና በደኸየ ኑሮም ይገቡ ዘንድ ተገደዱ፤ በነዚህም ውስጥ በጥቂት ሺህ የሚቆጠሩ ካቶሊካውያን ነበሩ። አንዳንድ ካህናት የራሳቸውን ሕይወት በሚያሰጋ ሁኔታ ውስጥም አስገብተው ቢሆንም እንኳ በድብቃዊ ሁኔታ ለነዚህ ጀርመናውያን ካቶሊኮች ምሥጢራትን በማደል ያገለግሉ ነበር። በዚህ ሁኔታ አዘውትረው ይመጡ ከነበሩት ካህናት መካከል እ.ኤ.አ. በጥቅምት 1963 ዓ.ም. ካራጋንዳ በሚባል አካባቢ አቅራቢያ በሰማዕትነት ያረፉት ዩክሬናዊው ካህን አባ አሌክሲጅ ሳሪትስኪ ይገኙበታል፤ እኚሁ ካህን እ.ኤ.አ. በ2001 ዓ.ም. በቅ. ዮሐንስ ጳውሎስ ዳግማዊ ብፅእናቸው ታውጇል።
እኚህን ሰማዕት ካህን በዚያ ሁኔታ ውስጥ እየመጡ ያገለግሏቸው የነበሩ ክርስቲያኖች ይወዷቸው ነበር እናም «የእግዚአብሔር ወሮበላ» ብለውም ይጠሯቸው ነበር። እ.ኤ.አ. ጥር 1958 ዓ.ም. በስደት ከሚኖሩበት አካባቢ በድንገት ተደብቀው ካዛክስታን ውስጥ ወዳለችው ወደ ካራጋንዳ ከተማ መጡ። አባ አሌክሲጅ በተቻለ መጠን ብዙ ምእመናን ይቆርቡ ዘንድ ያለምግብና ያለእንቅልፍ ቀን ከሌሊት ያናዝዙ ነበር፤ ምእመናኖቹም «አባ፣ መብላትና መጠጣት አለበዎት» ሲሏቸው የእርሳቸው መልስ «አልችልም፣ ምክንያቱም ፖሊሶች በየትኛውም ሰዓት ሊመጡ ይችላሉ፤ ይሄ ማለት ደግሞ መናዘዝና መቁረብ የነበረባቸው ሰዎች ይህን ሊያጡት ነው» የሚል ነበር።
መናዘዝ የሚፈልጉ ምእመናን ሁሉ ከተናዘዙ በኋላ አባ አሌክሲጅ መሥዋዕተ ቅዳሴ ማሳረግን እንደጀመሩ «ፖሊሶቹ መጡ!» የሚል ድምፅ አስተጋባ። በዚያ ከሚገኙት ምእመናኖቹ ውስጥ ማሪያ ሽኔይደር አንዷ ነበረችና አባን «እንሂድ አባ! እኔጋ ይደበቃሉ፤ እናምልጥ!» አለቻቸው። ስለዚህም ይህች ሴት አባን ከዚያ አካባቢ ራቅ ወዳለ አንድ ቤት ወስዳ በአንድ ክፍል እንዲሸሸጉ አደረገች፤ ወዲያውኑም ምግብ እያቀረበችላቸው «አሁን እንኳ መብላትና ትንሽም ማረፍ ይችላሉ፤ መሸትሸት ማለት ሲጀምር በአቅራቢያ ወደሚገኘው ከተማ እናመልጣለን» አለቻቸው። ቅዳሴ እንደተጀመረ ፖሊሶቹ በመምጣታቸው በመቋረጡ ምንም እንኳ ሰዎቹ የተናዘዙ ቢሆንም ባለመቁረባቸው ምክንያት አባ አሌክሲጅ አዝነዋል። ማሪያ «አባ! ምእመናኖቹ ሁሉ በትልቅ እምነትና መንፈሳዊነት መንፈሳዊ ቁርባን ይሳተፋሉ፤ ሌላ ጊዜ ደግሞ ተመልሰው እንደሚያቆርቡን ተስፋ እናደርጋለን» አለቻቸው።
ዕለቱ ማመሻሸት ሲጀምር ለሽሽቱ ዝግጅት ተጀመረ፤ ማሪያ የሁለት ዓመትና የስድስት ወር ልጆቿን ከእናቷ ጋር በቤቷ ትታ ፑልኬሪያ የተባለች ሌላ ሴት ዘመዷን በመጥራት አባ አሌክሲጅን በጫካ ውስጥ ከዜሮ በታች ሠላሳ ዲግሪ በሆነ ከባድ በረዷማ ቅዝቃዜ አሥራ ሁለት ኪ.ሜ. በመጓዝ ወደተባለችው ከተማ ሦስቱም ደረሱ። በዚያም ወደ አንድ ባቡር ጣቢያ ሄደው ሁለቱ ሴቶች ለአባ የጉዞ ቲኬትን ገዙላቸው፤ በመጠበቂያ ክፍልም ባቡሩን መጠበቅ ጀመሩ። አንድ ፖሊስ ወደዚያ ክፍል ገባና በቀጥታ አባን «ወዴት እየሄዱ ነው?» ብሎ ሲጠይቃቸው አባ ከድንጋጤ የተነሣ በፍጥነት መልስ መስጠት አልተቻላቸውም ነበር። ይህም የሆነው ስለራሳቸው ሕይወት ያይደለ አብራቸው ስላለችው የልጆች እናት የሆነችው ወጣቷ ስለማሪያ ሕይወት እጣ ፈንታ በማሰብ ነበር። ይህች ወጣት ራሷ ለፖሊሱ «እሳቸው ወዳጃችን ናቸው፤ እኛም እየሸኘናቸው ነው፤ ይኸው ቲኬታቸውን ተመልከት» በማለት ቲኬቱን ሰጠችው። ፖሊሱም ቲኬቱን ከተመለከተ በኋላ አባን «የባቡሩ የመጨረሻ ፉርጎ በሚቀጥለው ፌርማታ ተገንጥሎ ስለሚቀር እዚያ ላይ እንዳይሳፈሩ! መልካም ጉዞ!» በማለት ክፍሉን ለቆ ወጣ። አባ አሌክሲጅም ማሪያን እየተመለከቱ እንዲህ አሏት «እግዚአብሔር መልአክ አድርጎ አንቺን ላከልኝ! ለእኔ ያደረግሽውን በፍጹም አልረሳውም፤ የአምላክ ፈቃድ ከሆነ ሁላችሁንም ለማቁረብ ተመልሼ እመጣለሁ፤ በእያንዳንዷም ቅዳሴዬ ላንቺና ለልጆችሽ እጸልያለሁ።»
ይህ ከሆነ ከአንድ ዓመት በኋላ ማሪያ ወደምትገኝበት ወደ ክራስኖካምስክ አባ አሌክሲጅ መመለስ ቻሉ፤ አሁን መሥዋዕተ ቅዳሴ መቀደስና ምእመናንን ማቁረብ ችለዋል። ማሪያ ግን አባን አንድ ውለታ ያደርጉላት ዘንድ ጠየቀቻቸው፤ እንዲህ ብላ «አባ! እናቴ በጣም ታማ ነው ያለችው፣ ከመሞቷ በፊት ትቆርብ ዘንድ ለርሷ የሚሆን ቅ.ቁርባንን ሊሰጡኝ ይችሉ ይሆን?» አባም ማሪያ ለእናቷ የሚቻላትን ጥንቃቄ ሁሉ አድርጋ በሚገባው ክብር ማቁረብ የምትችል ከሆነ ጠይቀዋት ተስማምተው ቅ. ቁርባንን ሰጧት። ማሪያም የታመሙ እናቷን ለማቁረብ በእጇ ላይ ነጭ ጓንት አጠለቀች፣ ቅ. ቁርባኑን በወረንጦ ነገር ይዛም አቆረበቻቸው፤ ከዚያም በኋላ ተጠቅልሎበት የነበረውን ወረቀት አቃጠለችው።
የማሪያና የፑልኬሪያ ቤተሰቦች ወደ ኪርጊሰታን መኖሪያቸውን ቀየሩ። እ.ኤ.አ. በ1962 ዓ.ም. አባ አሌክሲጅ ወደዚች ከተማ በድብቅ መጥተው ማሪያና ፑልኬሪያን አገኟቸው፤ አንዴ በማሪያ ሌላ ጊዜም በፑልኬሪያ ቤት ቀደሱ። አባም በዚያ በረዷማ መሽት ያን ሁሉ አደጋ ተጋፍጠው የሸኟቸውን የእምነት ውለታ አስታውሰው፤ ከግልጽ መመሪያ ጋር ለፑልኬሪያ ቅ. ቁርባንን ትትውላት ለመሄድ ወሰኑና እንዲህ አሏት «ቅ. ቁርባንን ትቼልሽ እሄዳለሁ፤ ለዘጠኝ ተከታታይ ወራት በመጀመሪያዎቹ ዓርቦች ለኢየሱስ ቅዱስ ልብ አክብሮት መንፈሳዊነትን አድርጉ። የወሩ መጀመሪያ ዓርብ ሲሆን በቤትሽ ቅ. ቁርባንን በመግለጥ በሚታይ መልኩ ከፍ አድርገሽ በማስቀመጥ በሁሉ ነገሮች ታማኝ የሆኑና ምሥጢር የሚጠብቁ ምእመናንን ጠርተሽ አብራችው እንዲሰግዱ ጋብዢ። ዘጠኝ ወር በዚህ መልኩ ከተካሄደ በኋላ ቁረቢው፤ ግን በጥልቅ አክብሮት ይሁን።» እንደተነገራት ሁሉ ነገር ተከናወነ። ለዘጠኝ ወራት በዚያ ቤት ድብቅ የቅ. ቁርባን ስግደት ተደረገ፤ ማሪያም ከሰጋጅ ሴቶች አንዷ ነበረች።
እነዚህ ቅ. ቁርባናዊ ሴቶች (ለቅ. ቁርባን ልዩ መንፈሳዊነትና አክብሮት የነበራቸው ሴቶች) በዚያ ቅዱስ ቁርባን ፊት በአምልኮ በሰገዱ ቁጥር ጥልቅ የሆነ የመቁረብ ምኞት ነበራቸው። ሆኖም ግን ይህ ፍላጎት የነበራቸው ሴቶች ቁጥርና የቅ. ቁርባኑ ብዛት ያለመመጣጠን ይህን አልፈቀደም፤ አባ አሌክሲጅ በዘጠነኛው ወር መጨረሻ ላይ ፑልኬሪያ ብቻ እንድትቆርብና የተቀሩት ደግሞ መንፈሳዊ ተሳትፎ እንዲያደረጉ የወሰኑበት ምክንያትም ይኸው ነበር። ይህም ቢሆን እነዚህ ሴቶች ሁሉ ለቅ. ቁርባን ያላቸው መሰጠት ልዩ ነበር፤ ሁሉም ለልጆቻቸው የቅ. ቁርባንን ጥልቅ እምነት ልክ እንደ እናታዊ ወተት ለልጆቻቸው ለማስተላለፍ በቅተዋል።
(ይቀጥላል)