እኛ ማነን

በኢትዮጵያ ካቶሊካዊት ቤተክርስቲያን ሥር የምንገኝ ሲታውያን መነኮሳን በአገራችን በአዲስ አበባ፣ በመንዲዳ፣ በሆሣዕናና በጎንደር ገዳማት ሲኖሩን፤ ዓላማችንም በወንጌል ላይ የተመሠረተውን የቅዱስ አቡነ ቡሩክ ደንብን (The Rule of St. Benedict) በመከተል ክርሰቲያናዊ የጥምቀት ጸጋችንን በምልአት በሲታዊ ትውፊት መኖር ነው።.....

ይህም በምንኩስና ሕይወታችን፤ በግላዊም ሆነ ማኅበራዊ ጸሎትና ሥራ በቀጣይነት እግዚአብሔርን የመፈለግና የማመስገን ሕይወት ነው። በአጭር ቃላት ሕይወታችን “ጸሎትና ሥራ” (Ora et Labora) በሚለው ዘመን ጠገብ ትውፊታችን ይገለጻል።

ለዚህም ግብ መሳካት “ከክርስቶስ ፍቅር ምንም ነገር ያለማስበለጥ” የሚለውን ደንባችንን በማሰላሰል ለእግዚአብሔር መንግሥት መስፋትና ምስክርነት በጸጋው ተማምነን ለመኖር የወሰንን ነን።

በካቶሊክ ቤተ ክርስቲያን እምነት መንፈሳዊ ትምህርቶች፣ የመጽሐፍ ቅዱስ ጥናት፣ ታሪክ፣ ሥርዓተ አምልኮ፣ ጸሎቶችና መንፈሳዊነትን ወደ ምንካፈልበት፤ የቤተ ክርስቲያናችን ዜና ወደ ሚነገርበት፣ እንዲሁም በተቀደሰ ጋብቻም ሆነ በምንኩስና ሕይወት ወደ ቅድስና ጥሪ ለመጓዝ የሚያግዙ እውነታዎች ወደሚጋሩበት፣ የቅዱሳን ሕይወት፣ ሀብትና ትሩፋት ወደ ሚነገርበት፣ ባጠቃላይ የአምላካችን መልካም ዜና ወደሚታወጅበት ይህ ድረ ገጽ እንኳን በደህና መጡ!!

ከመ በኲሉ ይሴባሕ እግዚአብሔር!- እግዚአብሔር በነገር ሁሉ ይከብር ዘንድ፤ አሜን።1ጴጥ.4:11

Map St Joseph Cistercians

Top Panel

ሆሳዕና

ሆሳዕና

ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ “ሌላ ቀን እንደ ተራ ሰው ሆኖ ወደ ኢየሩሳሌም ይገባ ነበር፡፡ በዚህ ቀን ግን የአይሁድ ንጉሥ ሆኖ በክብር ገባ፡፡ ከቢታንያ ተነሥቶ ደብረ ዘይት ሲደርስ ከሐዋርያቱ ሁለቱን በቤተፋጌ ሰው ተቀምጦባት የማያውቅ ውርንጭላ እንዲያመጡለት ላካቸው፡፡ “በፊታችሁ ወዳለችው ሀገር ሂዱና ሰው ተቀምጦባት የማያውቅ የአህያ ውርንጫ ታገኛላችሁ፤ ፈትታችሁም አምጡልኝ፡፡ ባለቤቶቹ ቢጠይቋችሁ ጌታችን ፈልጓት ነው በሏቸው” አላቸው፡፡ ማቴ.21፡1-17

ወደ ቤተፋጌም ሄደው አህያዪቱን አገኙአት፡፡ ሲፈቱአትም ሳለ ባለቤቶቹ መጡባቸውና አስቆሟቸው፡፡ እነርሱም ኢየሱስ እንደፈለጋት ነገሩአቸው፡፡ ባለቤቶቹ ይህንን ሲያውቁ ተውአቸው፡፡ ሐዋርያትም የአህያዪቱን ውርንጭላ ፈትተው ወደ ኢየሱስ ወሰዱ፡፡ አጠገቡም ሲደርሱ ልብሳቸውን በአህያዪቱ ውርንጭላ ላይ አንጥፈው ኢየሱስን አስቀመጡት፡፡

“የጽዮን ልጅ ሆይ አትፍሪ እነሆ ንጉሥሽ በአህያ ውርንጭላ ላይ ተቀምጦ ይመጣል” ዘካ.9፡9 የሚለው የዘካርያስ ትንቢት ተፈጸመ፡፡ ሕዝቡም ኢየሱስ በመምጣት ላይ እንዳለ ሲያውቅ ሊቀበለው ወጣ፡፡ አንዳንዶች ያልፍበት በነበረ መንገድ ልብሳቸውን እንዳንዶቹ ደግሞ የዘንባበ ዝንጣፊ ያነጥፉ ነበር፡፡ ከፊትና በኋላ ያሉት ደግሞ “ሆሳዕና በጌታ ስም የሚመጣ የተባረከ ነው፤ ሆሳዕና ለዳዊት ልጅ” እያሉ በታላቅ ድምፅ ይጮሁ ነበር፡፡ ኢየሱስ በሕዝቡ እልልታና ደስታ ታጅቦ ሲገባ ተጠንቅቀው ይታዘቡትና ይመለከቱት የነበሩ ፈሪሳውያን ደቀ መዛሙርቱን ዝም እንዲያሰኛቸው ተናገሩት፡፡ እርሱም ሕዝቡ ዝም ቢል ድንጋዮች እንደሚጮኹ አስታወቃቸው፡፡ ኢየሱስ ኢየሩሳሌምን ሲያያት አለቀሰላት፡፡ “አንቺ ኢየሩሳሌም ለሰላምሽ የሚያስፈልገውን ነገር ምነው አውቀሽ ቢሆን ኖሮ አሁን ግን ይህ ነገር ከዓይንሽ ተሰውሮብሻል ጠላቶችሽ በዙሪያሽ እንደ አጥር ከብበው በዚህም በዚያም አንቺን የሚያስጨንቁበት ጊዜ ይመጣል… ምክንያቱም እግዚአብሔር ሊያድንሽና ሊጐበኝሽ የመጣበትን ጊዜ ባለማወቅሽ ነው” እያለ ረገማት፡፡

ኢየሱስ ወደ ኢየሩሳሌም የገባው ሰለ ደኅንተቷ ሊያሳስባት ፈልጐ ነው፡፡ በማያወላዳ መንገድ ንጉሷና መድኃኒቷ እንደሆነ ገለጸላት፡፡ ወደ ራሷ ተመልሳ ጸጋዋን እንድትቀበል የልቧን ድንዳኔ ትታ እርሱን እንድትሰማ አስጠነጠቃት፡፡ ግን አልተጠነቀቀችም፡፡ ለጊዜው በክብር ተቀበለችው፡፡ ከጥቂት ቀን በኋላ ግን ተወችው፤ በመስቀል ላይ ሰቀለችው፡፡ የደኅንነቷን ቀን ማወቅ ተሳናት፡፡ በዚህም ደግሞ ከብዙ ዓመታት በኋላ መዓት ወረደባት፡፡

ይህ የሚያሳዝን የኢየሩሳሌም ሥራ የእኛም ሥራ ነው፡፡ ኢየሱስን መድኃኒታችንን መቀበል አንፈልግም ወይም ተቀብለን በኃጢአታችን ከእኛ እንዲርቅ እናደርገዋለን፡፡ በቅዱስ ቁርባን ወደ እኛ ሲመጣ በደስታ እንቀበለዋለን፡፡ ትንሽ ቆየት ብለን ደግሞ እናዋርደዋለን፡፡ ከእርሱ ጋር እንጣላለን፡፡ ከኃጢአት ጋር ጓደኝነት እንይዛለን፡፡ በኃጢአት ስንወድቅ እርሱን እንደገና እንሰቅለዋለን፡፡ ኢየሱስ እኛን “አቤት በዚህ ቀን ለደኅንነትህ የሚደረገውን ብታውቅ ኖሮ …፣ ይህ ሁሉ ከዓይንህ ተሰውሮብሃል ማወቅን አልፈለግህም፡፡ ይህን እወቅ ግን አንድ ቀን …” እያለ አዝኖ ይፈርድብናል፡፡ ይህንን በማሰብ ሲመጣና ሲናገረን እምቢ አንበለው አናባርረው፡፡ በኋላ እርሱ ቂም ይዞ እምቢ እንዳይለና እንዳያባርረን ደኅንነታችንን ራሳችን አናጥፋት፡፡

ምንጭ:- መንፈሳዊ ማሳሰቢያ - የእለቱ አስተንትኖ

አድራሻችን

logo

                 ገዳመ ቅዱስ ዮሴፍ ዘሲታውያን

                    ፖ.ሳ.ቁ. 21902
                 አዲስ አበባ - ኢትዮጵያ
             Phone: +251 (116) 461-435

              Fax +251 (116) 458-988

               contact@ethiocist.org

             https://www.ethiocist.org

 
 

ለድረ ገጻችን የሚሆን ጽሑፍ ካለዎ

1- የኢሜል አድራሻችንን webpageorganizers@gmail.comን ተጠቅመው አሊያም

2- ይህን ሲጫኑ በሚያገኙት CONTACT FORMበሚለው ቅጽ ላይ ጽሑፍዎን ለጥፈው ወይም 

3-facebook አድራሻችን https://www.facebook.com/ethiocist.org በግል መልእከት ይላኩልን

በተጨማሪም የሚያካፍሉት ጠቃሚ የድረገጽ አድራሻ ካለዎ ይላኩልን።   

መልእክት ከር.ሊ.ጳ. ፍራንቼስኮስ

pope"ይቅርታን እና ምሕረትን ማድረግ የሰላማዊ ሕይወት መሠረት ነው"።

“ይቅር ማለት እና ምህረትን ማድረግ የሕይወት ዘይቤያችን ቢሆኑ ኖሮ፥ ስንት ጦርነት፣ ስቃይ እና መከራን እናስቀር ነበር! በግንኙነቶቻችን ሁሉ ይቅርታን የሚያደርግ ፍቅር ያስፈልጋል። ይኸውም በባል እና ሚስት፤ በወላጆች እና በልጆች መካከል እንዲሁም በአካባቢያችን፣ በማኅበረሰባችን እና በፖለቲካውም ማለት ነው። እንዲሁም ይቅርታን ለማድረግ ጥረት የማናደርግ ከሆነ፥ ይቅር አይባልልንም” ማለታቸው ተገልጿል።

ምንጭ - ቫቲካን ራድዮ አማርኛ ዝግጅት