እኛ ማነን

በኢትዮጵያ ካቶሊካዊት ቤተክርስቲያን ሥር የምንገኝ ሲታውያን መነኮሳን በአገራችን በአዲስ አበባ፣ በመንዲዳ፣ በሆሣዕናና በጎንደር ገዳማት ሲኖሩን፤ ዓላማችንም በወንጌል ላይ የተመሠረተውን የቅዱስ አቡነ ቡሩክ ደንብን (The Rule of St. Benedict) በመከተል ክርሰቲያናዊ የጥምቀት ጸጋችንን በምልአት በሲታዊ ትውፊት መኖር ነው።.....

ይህም በምንኩስና ሕይወታችን፤ በግላዊም ሆነ ማኅበራዊ ጸሎትና ሥራ በቀጣይነት እግዚአብሔርን የመፈለግና የማመስገን ሕይወት ነው። በአጭር ቃላት ሕይወታችን “ጸሎትና ሥራ” (Ora et Labora) በሚለው ዘመን ጠገብ ትውፊታችን ይገለጻል።

ለዚህም ግብ መሳካት “ከክርስቶስ ፍቅር ምንም ነገር ያለማስበለጥ” የሚለውን ደንባችንን በማሰላሰል ለእግዚአብሔር መንግሥት መስፋትና ምስክርነት በጸጋው ተማምነን ለመኖር የወሰንን ነን።

በካቶሊክ ቤተ ክርስቲያን እምነት መንፈሳዊ ትምህርቶች፣ የመጽሐፍ ቅዱስ ጥናት፣ ታሪክ፣ ሥርዓተ አምልኮ፣ ጸሎቶችና መንፈሳዊነትን ወደ ምንካፈልበት፤ የቤተ ክርስቲያናችን ዜና ወደ ሚነገርበት፣ እንዲሁም በተቀደሰ ጋብቻም ሆነ በምንኩስና ሕይወት ወደ ቅድስና ጥሪ ለመጓዝ የሚያግዙ እውነታዎች ወደሚጋሩበት፣ የቅዱሳን ሕይወት፣ ሀብትና ትሩፋት ወደ ሚነገርበት፣ ባጠቃላይ የአምላካችን መልካም ዜና ወደሚታወጅበት ይህ ድረ ገጽ እንኳን በደህና መጡ!!

ከመ በኲሉ ይሴባሕ እግዚአብሔር!- እግዚአብሔር በነገር ሁሉ ይከብር ዘንድ፤ አሜን።1ጴጥ.4:11

Map St Joseph Cistercians

Top Panel

22.2 - የመንፈስ ቅዱስና የእሳት ጥምቀት የሚባለው ነገር ምንድነው?

(ካለፈው የቀጠለ)

Menfes Kidusእስካሁን እንዳየነው "የመንፈስ ቅዱስና የእሳት ጥምቀት" የሚለው አባባል በመሠረቱ መጽሐፍ ቅዱሳዊ (biblical) አባባል ነው፡፡ የሚያመለክተውም የመንፈስ ቅዱስን በምእመናን ላይ መውረድ ነው፡፡ በመንፈስ ቅዱስ እና በእሳት የሚያጠምቀው ራሱ ጌታ ኢየሱስ ነው፡፡ ለመጀመሪያ ጊዜም ይህ ዓይነቱ ጥምቀት ሲፈፀም የምናየው በበዓለ-ሃምሣ ዕለት ነው፡፡ የሐዋ.ሥራ 2፡1-4 ላይ የተገለጸው የበዓለ-ሃምሣው ድራማ (ተፈጻሚት) የቃሉን ትክክለኛነት በተጨባጭ ያረጋግጥልናል፡፡ "... እንደ እሳትም የተከፋፈሉ ልሳኖች ታዩአቸው፤ በያንዳንዳቸውም ላይ ተቀመጡባቸው፡፡ በሁሉም መንፈስ ቅዱስ ሞላባቸው..." (ቁ.3-4)

የኢየሱስ እናት ማርያምና ሐዋርያት ሌሎች አማንያንም ባንድ ልብ ተሰበብስበው በጸሎት ላይ እንዳሉ በመንፈስ ቅዱስ ድንገት ይሞላሉ፤ መንፈስ ቅዱስ በያንዳንዳቸው ላይ ያረፈው በእሳት ነበልባል (እንደ እሳት የተከፋፈሉ ልሳኖች) አምሳያነት ነበር፡፡ "የመንፈስ ቅዱስና የእሳት ጥምቀት" የሚለው አገላለጽ ቃል ለቃሉ ሲፈጸም የምናገኘውም በዚሁ ጥቅስ ውስጥ ነው፡፡ ከዚህ በኋላ ግን "በመንፈስ ቅዱስ" መጠመቅ የሚል አገላለጽ ብቻ በሐዋርያት ሥራ ላይ ሲዘወተር እናያለን፡፡ እንዲሁም ይህን አገላለጽ "በመንፈስ ቅዱስ መሞላት" (የሐዋ.ሥራ 4፡31) "መንፈስ ቅዱስን መቀበል (የመንፈስ ቅዱስ መሰጠት)" (የሐዋ. 8፡15) "የመንፈስ ቅዱስ መውረድ" (የሐዋ.ሥራ 8፡16፤ 10፡44፤ 11፡15) በሚሉ ተመሳሳይ አገላለጾች በተወራራሽነት ሲተካ እናገኛለን፡፡ ይህም የሚያረጋግጥልን፥ "በመንፈስ ቅዱስ መጠመቅ" ወይም "በእሳትና በመንፈስ ቅዱስ መጠመቅ" የሚባለው ነገር "በመንፈስ ቅዱስ መሞላትን" የሚገልጽ አባባል እንደሆነ ነው፡፡

ያነበብናቸው ጥቅሶች እንደሚያሳዩት፥ የመንፈስ ቅዱስ ጥምቀት ከዮሐንስ ጥምቀት የተለየ ነው፡፡ በሌላ በኩል ግን በጌታ ኢየሱስ የተመሠረተው ምስጢረ ጥምቀት (ወይም አስቀድመን እንዳየነው ሳክራሜንታል ባፕቲዝም)፥ ከመንፈስ ቅዱስና እሳት ጥምቀት ጋር የሚጋጭ ነገር አይደለም፡፡ አብረው የሚመጡ አንዳንዴም አንዱ ከሌላው ቀድሞ የሚከሰቱ ነገሮች ናቸው፡፡ በሁለቱም አማካይነት መንፈስ ቅዱስ ይወርዳል፤ ምእመናንን ይሞላል፣ ይቀድሳል፣ ኃይልም ይሰጣቸዋል፡፡ በመሠረቱ ሁለቱም አብረው የሚከሰቱ ናቸው፡፡ ለምሳሌ ጌታ ኢየሱስ እንደተጠመቀ ወዲያውኑ መንፈስ ቅዱስ በርግብ አምሳል በርሱ ላይ መውረዱ ይህን ያረጋግጣል፡፡ እዚህ ላይ ግን ማስታወስ የሚገባን የኛንና ጌታ ኢየሱስ የተጠመቀው ጥምቀትን ልዩነት ነው፡፡ እኛ ኃጢአታችን (ከአዳም የወረስነውን ይሁን ራሳችን የሠራነውን) እንዲደመሰስልን እንጠመቃለን፤ ጌታ ኢየሱስ ግን ኃጢአት ስላልሠራ ይህ አያስፈልገውም ነበር፡፡ አጥማቂው ዮሐንስም ሌሎችን ሲያጠምቅ፥ አስቀድሞ ኃጢአታቸውን እንዲናዘዙ ያደርጋቸው ነበር፡፡ ከጌታ ኢየሱስ ግን ይህን ሊጠይቅ ስላልቻለ፥ ሊያጠምቀው እንደማይችል፣ እንዲያውም በኢየሱስ መጠመቅ የሚገባው እርሱ እንደሆነ በማመልከት ሲከለክለው ይታያል፡፡

በኢየሱስ ሐሳብ ተስማምቶ ሊያጠምቀው የፈቀደው፥ ኢየሱስ "አሁንስ ፍቀድልኝ እንዲህ ጽድቅን ሁሉ መፈጸም ይገባናልና" ያለው ጊዜ ነው (ማቴ. 3፡15) ኢየሱስ የተጠመቀው ለእኛ ምሳሌን (አብነትን) በገዛ ራሱ ሕይወት በማሳየት ጽድቅን ሁሉ ለመፈጸም ነበር፤ እኛ ግን ከኃጢአት ነፃ በመውጣት ይህን የጌታን ጽድቅ ለመቀበል ነው የምንጠመቀው፡፡ ልዩነቱ ይህ ነበር፡፡ በርግጥ ጌታ ኢየሱስ ከዘለዓለም እስከ ዘለዓለም ከመንፈስ ቅዱስ ጋር አብሮ የሚኖር አምላክ ነው፡፡ በሥጋ ባሕርይ እንደኛ ሆኖ መንፈስ ቅዱስን ሲቀበል የምናየው ግን ከጥምቀቱ ጋር ነው፡፡

የቅዱስ ጳውሎስን የለውጥ ታሪክ በምናነብበት ጊዜም ምስጢራዊ ጥምቀቱና የመንፈስ ቅዱስ ሙላቱ በአንድ ላይ እንደተፈጸመ (ወይም በአጭር ጊዜ ልዩነት ውስጥ እንደተከናወነ) እናያለን (የሐዋ.ሥራ 9፡17-19)

በሌላ በኩል ደግሞ ምስጢራዊ ጥምቀት ቀድሞ የመንፈስ ቅዱስ ጥምቀት ኋላ ሲከሰት የሚያመለክቱን ጥቅሶችም አሉ፡፡ በሐዋ. ሥራ 21፡8 ላይ ወንጌላዊ እንደነበረ የተነገረለት ከሰባቱ ዲያቆናት አንዱ የነበረው ፊልጶስ ለሰማርያ ነዋሪዎች ወንጌልን ከሰበከላቸው በኋላ፥ በጌታ በማመናቸው አጠመቃቸው (ከተጠመቁ መንፈስ ቅዱስን ተቀብለዋል ማለት ነው)፡፡ ነገር ግን በጰራቅሊጦስ ዕለት በሐዋርያት ላይ የወረደውን የእሳት ጥምቀት ገና በሕይወታቸው አልተለማመዱትም ነበር፡፡ ስለዚህ ጴጥሮስና ዮሐንስ ከኢየሩሳሌም ወደ ሰማርያ ወርደው ይህ እንዲፈጸም ጸለዩላቸው፡፡ ሰዎችም ይህን ተለማመዱ፡፡ "በዚያን ጊዜ እጃቸውን ጫኑባቸው መንፈስ ቅዱስንም ተቀበሉ" (የሐዋ.ሥራ 18፡17)፡፡ ጴጥሮስና ዮሐንስ ያደረጉት አሁን ጳጳሳት ሲያደርጉት የምናየውን ነው፡፡ ምስጢረ ሜሮንን የሚፈጽሙት ጳጳሳት ናቸው፡፡ በምእመናኑ ላይ እጃቸውን ጭነው ይጸልያሉ፤ ምእምናኑም በመንፈስ ቅዱስ ይሞላሉ፡፡ ከዚያ በፊት ግን መንፈስ ቅዱስን አልተቀበሉም ማለት አይደለም፤ ሲጠመቁ በመንፈስ ቅዱስ ተሞልተዋል፡፡

ፊልጶስ ዲያቆን ነበር፤ ስለዚህ ምስጢረ ሜሮንን ለማደል የግድ ጳጳስ መጥራት ነበረበት፡፡ ስለዚህም የመጀመሪያዎቹን ጳጳሳት ጴጥሮስንና ዮሐንስን በኢየሩሳሌም የነበረችው ቤተ ክርስቲያን ላከችለት፤ እነርሱም ይህን ተልእኮ ተወጡ፡፡ እዚህ ላይ እንደሚታየው፥ በነጴጥሮስ እጅ መጫን ምእመናኑ በመንፈስ ቅዱስ መሞላታቸው ምስጢረ ሜሮን ከመጀመሪያው ዘመነ ክርስትና ጀምሮ በተግባር ላይ የዋለ ምስጢር መሆኑን ነው፡፡ በዚህ ምክንያት፥ ይህን ሁኔታ፥ "የመንፈስ ቅዱስ ጥምቀት" ከሚለው አባባል ይልቅ "የምስጢረ ሜሮን አፈጻጸም" የሚለው አገላለጽ የበለጠ ያብራራዋል፡፡

(ይቀጥላል)

በኣባ ኤፍሬም ዓንዶም

አድራሻችን

logo

                 ገዳመ ቅዱስ ዮሴፍ ዘሲታውያን

                    ፖ.ሳ.ቁ. 21902
                 አዲስ አበባ - ኢትዮጵያ
             Phone: +251 (116) 461-435

              Fax +251 (116) 458-988

               contact@ethiocist.org

             https://www.ethiocist.org

 
 

ለድረ ገጻችን የሚሆን ጽሑፍ ካለዎ

1- የኢሜል አድራሻችንን webpageorganizers@gmail.comን ተጠቅመው አሊያም

2- ይህን ሲጫኑ በሚያገኙት CONTACT FORMበሚለው ቅጽ ላይ ጽሑፍዎን ለጥፈው ወይም 

3-facebook አድራሻችን https://www.facebook.com/ethiocist.org በግል መልእከት ይላኩልን

በተጨማሪም የሚያካፍሉት ጠቃሚ የድረገጽ አድራሻ ካለዎ ይላኩልን።   

መልእክት ከር.ሊ.ጳ. ፍራንቼስኮስ

pope"ይቅርታን እና ምሕረትን ማድረግ የሰላማዊ ሕይወት መሠረት ነው"።

“ይቅር ማለት እና ምህረትን ማድረግ የሕይወት ዘይቤያችን ቢሆኑ ኖሮ፥ ስንት ጦርነት፣ ስቃይ እና መከራን እናስቀር ነበር! በግንኙነቶቻችን ሁሉ ይቅርታን የሚያደርግ ፍቅር ያስፈልጋል። ይኸውም በባል እና ሚስት፤ በወላጆች እና በልጆች መካከል እንዲሁም በአካባቢያችን፣ በማኅበረሰባችን እና በፖለቲካውም ማለት ነው። እንዲሁም ይቅርታን ለማድረግ ጥረት የማናደርግ ከሆነ፥ ይቅር አይባልልንም” ማለታቸው ተገልጿል።

ምንጭ - ቫቲካን ራድዮ አማርኛ ዝግጅት