እኛ ማነን

በኢትዮጵያ ካቶሊካዊት ቤተክርስቲያን ሥር የምንገኝ ሲታውያን መነኮሳን በአገራችን በአዲስ አበባ፣ በመንዲዳ፣ በሆሣዕናና በጎንደር ገዳማት ሲኖሩን፤ ዓላማችንም በወንጌል ላይ የተመሠረተውን የቅዱስ አቡነ ቡሩክ ደንብን (The Rule of St. Benedict) በመከተል ክርሰቲያናዊ የጥምቀት ጸጋችንን በምልአት በሲታዊ ትውፊት መኖር ነው።.....

ይህም በምንኩስና ሕይወታችን፤ በግላዊም ሆነ ማኅበራዊ ጸሎትና ሥራ በቀጣይነት እግዚአብሔርን የመፈለግና የማመስገን ሕይወት ነው። በአጭር ቃላት ሕይወታችን “ጸሎትና ሥራ” (Ora et Labora) በሚለው ዘመን ጠገብ ትውፊታችን ይገለጻል።

ለዚህም ግብ መሳካት “ከክርስቶስ ፍቅር ምንም ነገር ያለማስበለጥ” የሚለውን ደንባችንን በማሰላሰል ለእግዚአብሔር መንግሥት መስፋትና ምስክርነት በጸጋው ተማምነን ለመኖር የወሰንን ነን።

በካቶሊክ ቤተ ክርስቲያን እምነት መንፈሳዊ ትምህርቶች፣ የመጽሐፍ ቅዱስ ጥናት፣ ታሪክ፣ ሥርዓተ አምልኮ፣ ጸሎቶችና መንፈሳዊነትን ወደ ምንካፈልበት፤ የቤተ ክርስቲያናችን ዜና ወደ ሚነገርበት፣ እንዲሁም በተቀደሰ ጋብቻም ሆነ በምንኩስና ሕይወት ወደ ቅድስና ጥሪ ለመጓዝ የሚያግዙ እውነታዎች ወደሚጋሩበት፣ የቅዱሳን ሕይወት፣ ሀብትና ትሩፋት ወደ ሚነገርበት፣ ባጠቃላይ የአምላካችን መልካም ዜና ወደሚታወጅበት ይህ ድረ ገጽ እንኳን በደህና መጡ!!

ከመ በኲሉ ይሴባሕ እግዚአብሔር!- እግዚአብሔር በነገር ሁሉ ይከብር ዘንድ፤ አሜን።1ጴጥ.4:11

Map St Joseph Cistercians

Top Panel

ክፍል 9 - የቅዱስ አውጎስጢኖስ ሥነ ጽሑፋዊ አበርክቶ

የቅዱስ አውጎስጢኖስ ሥነ ጽሑፋዊ አበርክቶ

ቅዱስ አውጎስጢኖስ በጊዜው ቤተክርስቲያንን በስብከቱና ትምህርተ ክርስቶስን በሚመለከት ጽሑፎቹ እየጠነከረች እንድትሄድ አድርጎአታል። የአጎስጢኖስ ብዕር ያልተወረወረበትና ቀለሙ ያልነጠበበት የነገረ መለኮት ክፍል ባይኖርም፤ በተለይ መለኮታዊ ጸጋን በሚመለከት ረገድ ተወዳዳሪ የለውም። 113 የሚሆኑ መጻሕፍትንና ድርሳናትን ከ200 በላይ የሚሆኑ መልእክታትን ከ500 የሚበልጡ ቃለ ስብከትና አስተምህሮችን አውርሶ አልፏል። ግላዊ ሕይወቱና ጠባዩን በጽሑፎቹ ላይ ተጽዕኖ አለው ቢባልም እንኳ ሃይማኖትንና ቅድስናን በሚመለከት የነበረው አመለካከትና ግንዛቦት ጉልህና በጽኑ መሠረት ላይ የታነጸ መሆኑን የሚያሳይ ነው።

ቅዱስ አውጎስጢኖስ በጽሑፍ ላይበዚህ ሁሉ የሥነ ጽሑፍ ባሕር ውስጥ ሊዋኝ የተገደደው የጽሕፈት ሱስ ኖሮት ወይም ለራሱ ስምና ክብር ሳይሆን በልቡ ውስጥ የነበረ የእግዚአብሔር ፍቅር ሞልቶ ተትረፍርፎ በመፍሰሱ ነው።

አንድ የቤተክርስትያን ታሪክ ማስታወሻ ይህንን ሲገልጽ “…….አውጎስጢኖስ ለራሱ ዝናን ለማትረፍ ሳይሆን ለእግዚአብሔር ፍቅርና ለሰው ፍቅር ብሎ በልቡ ውስጥ በቅሎ በብዙ ሺሕ የሚቆጠር ፍሬን ያፈራ እውነትንና ጽድቅን የሚገልጽ አዲስ ሐሳብን በማቅረብና በሐሳቡም ስፋትና ጥልቀት በጊዜው የሚተካከለው አልነበረም” ይላል።

ከመጽሓፍቶቹ በተለይ ወደ ነፍስ ወከፍ ሰው (ግለሰብ) እጅ  በመድረሳቸው በጣም የገነኑት ግን ሁለት ናቸው። እነርሱም “የእግዚአብሔር ከተማ” (The City of God) እና “ኑዛዜ” (Confession) የተባሉት ናቸው።

“ኑዛዜ”  በሚል ርእስ አውጎስጢኖስ የጻፈው መጽሐፍ ከልጅነቱ ጀምሮ ወደ ክርስትና እስከ ተመለሰበት ጊዜ ያሳለፈውን ሕይወት ይገልጻል። በተለይ የዚህ መጽሐፍ ዓላማ አውጎስጢኖስ ውጫዊ ታሪኩንና ዜና መዋዕሉን መተረክ ብቻ ሳይሆን ወደ ውስጣዊ ሁኔታውና ሐሳቡን ወደመግለጽ ያዘነበለ ነው። ስለዚህ የአውጎስጢኖስ ሥነ ልቦናዊ (Psychological)፣ ሞራላዊና አእምሮአዊ (Intellectual) ሕይወቱን ያንጸባርቃል። እግዚአብሔር በአእምሮውና በልቡ ውስጥ ያሳደረበትን ታላቅ ምኞትና ወደኋላ  ይጎትተው የነበረ የደካማነት ስሜታዊነትን በአእምሮው ብርሃኑም የተፈላሰፈውን ሁሉ ይገልጻል፤ ያምናል፤ ይናዘዘዋልም። ማንነቱን ለማግኘት ብዙ ድንጋዮችን የሚፈነቃቅል የአንድ ወጣት መንፈሳዊ ጉዞ ነው ሊባል ይቻላል።

የምታርፍበት ወደብ በመፈለግ በባህር ውስጥ በማዕበል እየተንገላታች እንደምትጓዝ መርከብ ሁሉ የሰው ነፍስ ደግሞ እውነተኛ ወደብዋ የሆነውን እግዚአብሔርን እስክታገኝ ድረስ ምን የሚመስል ፈተናና አስቸጋሪ ጉዞን እንደምታልፍ፤ እርሱን ሳታገኝ እንደማታርፍ አውጎስጢኖስ የገዛ ራሱን ሕይወትና ሁኔታ እንደማስገንዘቢያ አድርጎ በማቅረብ ሲመሰክር ስሜቱንና ሥነጽሑፋዊ ችሎታውን አቀናብሮ የሰውን መንፈስ በሚቀሰቅስ አኳኋን በዚህ “ኑዛዜ” በተባለው መጽሐፉ ማንነቱን ገልጾታል።

ምንም እንኳ በቋንቋዎቻችን የተተረጎመ ባይኖርም በሌሎች አብዛኞቹ የዘመናችን ቋንቋዎች ተተርጉሞ ስለሚገኝ የቻለ እንዲያነበው አደራ እንላለን። አውጎስጢኖስ በዕድሜ በስሎ ወደኋላ በመመለስ ያለፈ ሕይወቱን የታዘበበት መስኮት ስለ ሆነ አረጋውያን ያለፈ ሕይወታቸውን የሚመዝኑበት፤ ወጣቶች ደግሞ የሕይወት ትግላቸውና ችግራቸው፣ የጉዟቸውም ብዥታ በብዙ ቅዱሳን ዘንድ የታየና የነበረ እንጂ በእነሱ ያልተጀመረ እንዲሁም መፍትሔም ያለው መሆኑን እንዲገነዘቡና ለአካሂዳቸውም የተረጋገጠ መመሪያ ሊሆን የሚችል መጽሐፍ ነው።

“የእግዚአብሔር ከተማ” (The City of God) የተባለው መጽሐፉም ደግሞ በምድራዊ መንግሥትና በሰማያዊ መንግሥት መካከል ያለውን ንጽጽርና ልዩነት የሚገልጽ ቢሆንም አውጎስጢኖስ “ስለ ታሪክና” “ስለ ታሪክ ጉዞ” የነበረው ክርስቲያናዊ ፍልስፍናና አስተያየትን አብራርቶ የሚያንጸባርቅ ነው።

የምሥራቃዊ ቤተክርስቲያን አበውና ሊቃውንት የእግዚአብሔርን ሁናቴ የክርስቶስን ባሕርያትና የቅድስት ሥላሴን ምስጢር ለመረዳትና ለማብራራት ጥረት እንዳደረጉ ሁሉ ቅዱስ አጉስጢኖስ ደግሞ ኃጢአትን፤ የእግዚአብሔር ጸጋን፤ ደኅንነነትን ስለሚመለከት ጉዳይና እንዲሁም በምድር ላይ በመታግል ላይ የምትገኘው ቤተክርስቲያን ልታደርጋቸው የሚያስፈልጉዋትን ነገሮች ለመረዳት ብርቱ ጥረት አድርጓል።

ቅዱስ አውጎስጢኖስ ጸጋንና ኃጢአትን ስለሚመለከት ጉዳይ የነበረው ግንዛቤ የሚታየው የእነዶናቱስ፣ ማኒና ፔላጊዩስ ትምህርትን ለመግታት ባደረገው ከፍተኛ ጥልቀትና ርቀት ባለው ምርምሩ ነው። አውጎስጢኖስ ሰው በአርአያ ሥላሴ ተፈጥሮ ክፉውንና ደጉን የሚለይበት አእምሮና ፈቃድን ተሰጥቶት ነበር፤ ከአዳም ውድቀት በኋላ ግን ይህን ስጦታ አጠፋው። የአዳም ኃጢአት ለዘሩ ሁሉ ተላልፏል፤ ሕጻናትም የወረሱት ኃጢአት ስላላቸው መጠመቅ አለባቸው፤ የሰው ልጅ በኃጢአት በመውደቁ ምክንያት በራሱ ጥረትና በሥራው ብቻ ድኅነትን ሊያገኝ ወደማይችልበት ሁኔታ ተጥሎአል። ድኅነት እግዚአብሔር ራሱ በክርስቶስ ቤዛነት ላመኑት የሚሰጣቸው ጸጋ ነው። ይህንንም ሃሳቡን ቀለል ባለ አባባል ሲገልጸው “በራሱ ፈቃድ የፈጠረህ እግዚአብሔር ያላንተ ፈቃድ አያድንህም” ይለናል። የእግዚአብሔር ጸጋና ሥራችን ተባብረው ድኅንትን ያስገኛሉ። ጸጋ በጎ ምግባርን የሚያፈራ (የሚያስገኝ) እና ሠናይ ምግባር ደግሞ ጸጋን ማዳበር ይገባዋል የሚለው የዚህ የታላቁ አፍሪቃዊ ቅዱስ መንፈስና ሚዛናዊው ትምህርቱ በሰው ልጅ ግላዊ ሕይወትም ሆነ ታሪክ ለዘለቄታ የብርሃን ፋና ሆኖ ያኖራል።

አድራሻችን

logo

                 ገዳመ ቅዱስ ዮሴፍ ዘሲታውያን

                    ፖ.ሳ.ቁ. 21902
                 አዲስ አበባ - ኢትዮጵያ
             Phone: +251 (116) 461-435

              Fax +251 (116) 458-988

               contact@ethiocist.org

             https://www.ethiocist.org

 
 

ለድረ ገጻችን የሚሆን ጽሑፍ ካለዎ

1- የኢሜል አድራሻችንን webpageorganizers@gmail.comን ተጠቅመው አሊያም

2- ይህን ሲጫኑ በሚያገኙት CONTACT FORMበሚለው ቅጽ ላይ ጽሑፍዎን ለጥፈው ወይም 

3-facebook አድራሻችን https://www.facebook.com/ethiocist.org በግል መልእከት ይላኩልን

በተጨማሪም የሚያካፍሉት ጠቃሚ የድረገጽ አድራሻ ካለዎ ይላኩልን።   

መልእክት ከር.ሊ.ጳ. ፍራንቼስኮስ

pope"ይቅርታን እና ምሕረትን ማድረግ የሰላማዊ ሕይወት መሠረት ነው"።

“ይቅር ማለት እና ምህረትን ማድረግ የሕይወት ዘይቤያችን ቢሆኑ ኖሮ፥ ስንት ጦርነት፣ ስቃይ እና መከራን እናስቀር ነበር! በግንኙነቶቻችን ሁሉ ይቅርታን የሚያደርግ ፍቅር ያስፈልጋል። ይኸውም በባል እና ሚስት፤ በወላጆች እና በልጆች መካከል እንዲሁም በአካባቢያችን፣ በማኅበረሰባችን እና በፖለቲካውም ማለት ነው። እንዲሁም ይቅርታን ለማድረግ ጥረት የማናደርግ ከሆነ፥ ይቅር አይባልልንም” ማለታቸው ተገልጿል።

ምንጭ - ቫቲካን ራድዮ አማርኛ ዝግጅት