ክፍል 6 - የአውጎስጢኖስ እናት ሞኒካ መሞት
- Category: የቅዱስ አውጎስጢኖስ የሕይወት ታሪክ
- Published: Thursday, 30 August 2012 10:58
- Written by Super User
- Hits: 2583
- 30 Aug
የአውጎስጢኖስ እናት ሞኒካ መሞት
አውጎስጢኖስ የክርስትናን እምነት ከተቀበለ በኋላ የአስተማሪነት ሥራውን ትቶ ወደ አፍሪካ ለመመለስ ከቤተሰቡ ጋር ተነሣ። ኦስቲያ በተባለ ወደብ ሆኖም መርከቦችን ለመጠበቅ ውሎ ማደር ግድ ሆነባቸው። በዚህ ጊዜ ሞኒካ እናቱ በጠና ታማ ሞት አፋፍ ላይ ደረሰች። በዚህ ሁኔታ ውስጥ እያለች በአገሯ መቀበር እንዳለባት ሲጠይቋት “የትም ይሁን የት ለእግዚአብሔር የሚሳነው ነገር የለም፤ በሙታን ትንሣኤ ጊዜ ጌታ ለፍርድ ሲመጣ እኔ የምነሣበትን ሥፍራ እርሱ ይስተዋል ብሎ ማሰብ አይቻልም” ብላ መለሰችላቸው።
አውጎስጢኖስ የቅድስት እናቱን የምድራዊ ጉዞ መጨረሻ ምዕራፎች እንዴት እንዳሳለፈች ሲመሰክር ሰፋ አድርጎ እንዲህ ገልጾታል፦
“ከዚህ ዓለም የምትለይበት (ሞኒካ) ጊዜ ሲደርስ አንተ ያወቅኸው እኛ ግን ያላወቅነው ቀን፤ አንተ ባዘጋጀኸው ምሥጢራዊ እቅድ በመሬት ላይ ካደረግነው ርጅምና አድካሚ ጉዞ ለባህር ጉዟችን ዕረፍት እይደረግን እኔና እርሷ ወደ አትክልት ቦታ አቅጣጫ ወዳለው መስኮት ተደግፈን ቆመን ነበር። እዚያ ሁለታችን ብቻ በጥልቅ ደስታ ተነጋገርን። ከኋላችን የተውናቸውን ነገሮች በመርሳት ከፊታችን ያለውን ነገር ተወያየን። እውነት የሆንህ ጌት አንተ ባለህበት ዓይን ያላየው፣ ጆሮ ያልሰማውና ወደ ሰው ልብ ውስጥም ያልገባው የቅዱሳን ዘለዓለማዊ ሕይወት ምን እንደሚመስል ማለትም ምን ሊመስል እንድሚችል ተጨዋወትን። ነገር ግን የልባችን አፍ ከፍተኛውን የምንጭህን ውሃ ካንተ ጋር ያለውን የሕይወት ምንጭ ተጠማ።…ጌታ ሆይ! ስለነዚህ ነገሮች በተነጋገርንበት ቀን ዓለምና በውስጧ ያለው ደስታ ሁሉ ከምንነጋገረው ጋር ሲነጻጸር በጣም ርካሽ እንደነበር አንተ ታውቃለህ። እናቴም “ልጄ ሆይ! በበኩሌ እዚህ ዓለም ውስጥ ከዚህ በላይ ምንም ደስታ አላገኝም፤ ከዚህ ዓለም ምንም ነገር ከአሁን በኋላ ስለማልጠብቅ እዚህ ምን እንደምሠራ ወይም ለምን እዚህ እንዳለሁ አላውቅም። በዚህ ሕይወት ለትንሽ ጊዜ መቆየት ፈልጌ የነበረበት ምክንያት አንተ ክርስቲያን ሆነህ ለማየት ነበር። ይህንንም እግዚአብሔር ፈቅዶ አንተ የዓለምን ደስታ ንቀህ የእርሱ አገልጋይ ለመሆን መብቃትህን አይቻለሁ። ታዲያ ምን እሠራለሁ?” አለችኝ።ምን ዓይነት መልስ እንደሰጠኋት በግልጽ ትዝ አይለኝም። ከዚህ በኋላ አምስት ቀን በማይሞላ ጊዜ ውስጥ ኃይለኛ ትኩሳት ያዛት። በዚህም በሽታዋ አንድ ቀን ለጥቂት ደቂቃዎች ራሷን ሳተች። ወደርሷ ሮጠን ደረስን፤ ነገር ግን ወዲያው ነፍሷን አወቀች። እኔና ወንድሜ አጠገቧ ቆመን በማየቷ በመደነቅ “የት ነኝ?” ብላ ጠየቀች። ከዚያም በኀዘን ሰምጠን ምንም ሳንናገር በመቆማችን ትኩር ብላ አይታን “እናታችሁን የምትቀብሩት እዚህ ነው” አለች። እኔ ምንም ሳልናገር ላለማልቀስ እታገል ነበር፤ ወንድሜ ግን በትውልድ አገሯ ብትቀበር እንደሚደሰት ተናገረ። ነገር ግን እናቴ በዚህ ጊዜ በጭንቀት ተመለከተችው፤ ንግግሩ የምድራዊ ነገሮች ቃና ስለነበረው በዓይኗ ልትገታው ሞከረች። ከዚያም እኔን ተመለከተችና “እንዴት እንደሚናገር ተመልከት” አለች። በኋላም ለሁለታችንም “ይህን አካል በየትም አኑሩት፤ ስለሱ አትጨነቁ!...ነገር ግን በያላችሁበት ቦታ በጌታ መንበረ ታቦት እንድታስቡኝ እለምናችኋለሁ” አለችን። በምታውቀውና በምትችለው መንገድ ይህን ምኞቷን ከተናገረች በኋላ በሽታዋ ስለበረታባት ጸጥ አለች።”
አውጎስጢኖስ በገለጸልን በዚህ አኳኃን ሞኒካ በ56 ዓመቷ በ 387 ዓ.ም. ኦስቲያ በሚባል ቦታ ጣልያን ውስጥ አረፈች።
ሞኒካ የመንግሥተ ሰማይ ወራሽ መሆኗ የማያጠራጥር ቢሆንም ሞት የሚፈጥረው ጊዜያዊ አካላዊ መለያየት ኀዘንን ያስከትላልና በተለይም የአውጎስጢኖስ ልጅ ወጣቱ አድዮዳቱስ ስለ አያቱ ሞት አምርሮ ሲያለቅስ ያዩት የአባቱ ጓደኞች “ምሕረተ ወፍትሐ አኀሊ ለከ፤ እዜምር ወእሌቡ ፍኖተ ንጹሐ…” (መዝ.50) ማለትም አቤቱ ምሕረትንና ፍርድን እቀኝልሃለሁ፤ ንጹሕ መንገድንም አስታውሳለሁ የሚል መዝሙር በበገና ታጅበው መዘመር ጀመሩ፤ አውጎስጢኖስ በበኩሉ በር ዘግቶ በአንድ ክፍል ቤት ውስጥ ያለቅስ ነበር መሪር ኀዘኑን “መላ ዕድሜዋን ላለቀሰችልኝ እናቴ ትንሽ ባለቅስላት እንደ ኃጢአት የሚቆጥርብኝ ይኖር ይሆን?...” በማለት በልቅሶ ይገልጽ ነበር። እናቱንም ከመንገድ ዳር ከቀበረ በኋላ ወደ ሰሜን አፍሪካ ተጓዘ። ከዚህ በኋላ ሁለት ጊዜ ሮማን ከመጎብኘቱ በስተቀር የተቀመጠው በትውልድ አገሩ በሰሜን አፍሪካ ነው። አባቱ ካወረሰው ንብረት ለኑሮው የሚሆነውን ብቻ አስቀርቶ ሌላውን ሁሉ በመሸጥ ለድኾች አከፋፈለው። ከዚያ በኋላ ከወዳጆቹ ጋር ሦስት ዓአት ያገኙትን በአንድነት በማድረግ በኅብረት መኖር ጀመሩ። በዚህ ጊዜ ከዓለማዊ ሐሳብ ተለይቶ በጸሎትና በመጻሕፍት ምርምር ተጠምዶ ክርስቲያናዊ ሕይወቱ እይበረታ በሄደ መጠን በሰቂለ ኅሊና የአምላክ ጸጋን ማሰላሰልና የተቀደሰ ሕይወትን መኖር ቀጠለ።
በአካባቢው ይኖሩ የነበሩ ምእመናን ሀብትን በሚመለከት ረገድ መስገብገብን ትተው እርስ በርስ በፍቅር እንዲተሳሰሩ መክሯቸዋል፤ አስተምሯቸዋልም። አውጎስጢኖስ ራሱ በንጽሕና ለመኖር ወሰነ፤ ብዙ ገዳማትንም ተከለ። በታጋስቴና በሂፖ አካባቢ ያቋቋማቸው ገዳማት ለአያሌ ዘመናት በሰሜን አፍሪካ አብያተ ክርስቲያናት ያገለገሉ ካህናትና ዲያቆናት እየተማሩ የሚወጡበት፤ የክህነት ጥሪም የሚያብብበት ሆኖ ቀጥሎ ነበር።